እንዳለመታደል ሆኖ ኢትዮጵያ ውስጥ ሕዝብ “ድምፄ የተከበረበትና በካርዴ የመረጥኩት መንግሥት ሥልጣን ያዘ” ብሎ የሚጠቅሰው የምርጫ ታሪክ የለውም። ሒደታቸውና ውጤታቸው የተለያየ ቢሆንም በአፄው ዘመንም ይሁን በደርግ፣ ከዚያም በኋላ በኢሕአዴግ የአስተዳደር ዘመናት በኢትዮጵያ የተካሄዱት ምርጫዎች ሁሉ የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት የተረጋገጠባቸው ምርጫዎች እንዳልነበሩ አፍን ሞልቶ መናገር ይቻላል። ይህችን አገር ወደ ዴሞክራሲ ሊያሸጋግሯት አቅም የነበራቸው ዕድሎች ሁሉ በአገዛዞቹ ኢ-ዴሞክራሲያዊ ባህሪ ምክንያት ባክነዋል። አሁን ባለንበት የፖለቲካ ሥርዓት ደግሞ “የሕዝብ የሥልጣን ምንጭነት ያልተከበረባቸው ያለፉት የምርጫ ሒደቶች ከዚህ በኋላ ፈጽሞ አይደገሙም” የሚል ቃል ተገብቷል። ለዚህ ቃል መከበር መገለጫ ይሆናል የተባለው ደግሞ መጪው አገራዊ ምርጫ ነው።
ኢሕአዴግ ደርግን ጥሎ መንበሩን ከያዘ ወዲህ ስድስተኛ የሆነው አገራዊ ምርጫ በመጪው ግንቦት ወር 2012 ዓ.ም. እንደሚካሄድ ተወስኗል። ምርጫ ቦርድ ይህንን ምርጫ በተወሰነለት የጊዜ ሰሌዳ ለማካሄድ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ተናግሯል። አንዳንድ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከወዲሁ የምርጫ ዝግጅትና ቅስቀሳ ጀምረዋል። ጥቂት የማይባሉት ፓርቲዎችም ከአንድ ሁለት መሆን ይበጃል ብለው ውህደት ፈጽመዋል። የተወሰኑ የሲቪክ ተቋማት ከምርጫው ጋር በተያያዙ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ መድረኮችን እያዘጋጁ ሕዝባዊ ውይይቶችን እያካሄዱ ነው። አንዳንድ የመገናኛ ብዙኃንም በምርጫ 2012 ላይ ያተኮሩ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት ለአድማጭ ተመልካቾቻቸው እያቀረቡ ይገኛሉ።
በሌላ በኩል ምርጫ ቦርድና ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሚገናኙባቸው መድረኮች በአዲሱ የምርጫና የፖለቲካ ፓርቲዎች አዋጅ ላይ መግባባት ተስኗቸው ስብሰባዎቻቸውን እየበተኑ ነው። የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀመንበር ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ይህ ሊፈታ ያልቻለ አለመግባባት ቦርዱ በሚያካሂደው የምርጫ ዝግጅት ላይ እንቅፋት መፍጠሩን በይፋ ተናግረዋል። ወዲህም ቦርዱ አዲሱን “የብልጽግና ፓርቲ” ጨምሮ እውቅና ለማግኘት የጠየቁ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ምዝገባ አጠናቆ አልጨረሰም። ጥቂት የማይባሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደግሞ በሚያቀርቧቸው ሥጋቶችና ቅድመ ሁኔታዎች ምክንያት ምርጫው እንዲዘገይ ተደጋጋሚ ጥያቄ እያቀረቡ ነው። በተቃራኒው ሥልጣን የያዘው አካል ምርጫውን በተያዘለት የጊዜ ገደብ ካላካሄደ ከሕገ መንግሥት ያፈነገጠ ሁኔታ ይፈጠራል ብለው ሌሎች እያስጠነቀቁ ነው። የፖለቲካ ፓርቲዎች ቅስቀሳ ቢጀምሩ እንኳን በየክልሎቹ በኢመደበኛ አደረጃጀቶች የሚፈጠሩ የሰላምና ደኅንነት ሥጋቶችም ከወዲሁ ሚዛን ደፍተው እያወያዩ ነው።
ያም ሆነ ይህ መጪው አገር አቀፍ ምርጫ በዋና ተዋናዮቹ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ይሁን በመራጩ ሕዝብ ዘንድ ከፍ ባለ ሥጋትም፣ ጉጉትም እየተጠበቀ ነው። ዋነኛው ጉዳይ ግን ምርጫው እንደተባለው በተያዘለት የጊዜ ገደብ የሚካሄድ ከሆነ ሰላማዊና ነፃ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ምን መደረግ አለበት የሚለው ቁምነገር ላይ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ወደ ሥልጣን ከመጡበት ወቅት ጀምሮ ምርጫውን በተመለከተ የሰነዘሯቸው ሐሳቦች “ጥቂት ፓርቲ፣ ከባድ ፉክክር እና ነፃ ምርጫ” በሚሉ ፍሬ ነገሮች የተጠቀለሉ ናቸው። ብዙዎች ግን ምርጫው ነፃነቱም፣ አፎካካሪነቱም እንዳለ ሆኖ ከባድ ሥራ በላቀ ትኩረት የሚፈልገው በሰላም መጠናቀቁ ላይ ነው ሲሉ ይመክራሉ። ምርጫው ሲነሳ የዜጎች ሥጋት ከማናቸውም ገቺ ሁኔታዎች ይልቅ በዚህ ላይ ትኩረቱን ያደርጋል።
እንደ ኢትዮጵያ ባለ የብሔር ክፍፍልና የርስ በርስ ግጭት የፖለቲካ መድረኩን በያዘባት አገር ሰላማዊ ምርጫ ለማካሄድ አስተማማኝ ሰላም እንዲሁም ከግጭት ብቻ ሳይሆን ከግጭት ሥጋት የጸዳ ከባቢ ያስፈልጋል። በመላው አገሪቱ ጥቃቅን ሁነቶችን ተግነው ድንገት ሲቀሰቀሱ የምናያቸው ግጭቶች በምርጫው ሰሞን እንዳይባባሱና ሰላምና መረጋጋት ወዳልተጠበቀ ሁኔታ እንዳይመሩት መጠንቀቅ ያስፈልጋል።
የ2012 ምርጫ የመጣው ኢትዮጵያ በመንታ መንገድ ላይ በቆመችበት ወቅት ነው። አሁን ያለንበትን ነባራዊ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ተጨባጭ ሁኔታ መሠረት አድርገን መጪውን ዘመን ካሰላን የአገራችን ዕጣ ፈንታ በሁለት ምርጫዎች ውስጥ ይወድቃል። አንድም የገጠሙ ፈተናዎችን በመነጋገር፣ በመተማመን እና በተባበረ ጥረት በመሻገር የኢትዮጵያን ንጋት ማብሰር፣ ወይም የዘር ክፍፍሉን፣ የብሔር ጽንፈኝነቱን እና የኔ ብቻ የሚለውን አስተሳሰብ ብቻ ይዞ በመጓዝ የአገሪቱንና የሕዝቧን መፃዒ ዕድል አደጋ ውስጥ መጨመር።
ሁሉም አካል ይህች አገር ከገጠማት መንታ መንገድ ውስጥ አንዱን ምረጥ ቢባል ወደ ሰላም፣ ዕድገትና ዴሞክራሲ የሚመራትን መንገድ ይዛ እንድትጓዝ ይሻል። በዚህ መንገድ ተጉዛ ለምትደርስበት ንጋት ዕውን መሆን ደግሞ በማናቸውም ልዩነቶች ላይ ውይይት ማድረግ፣ በችግሮች ላይ መነጋገርና በድርድር የሁሉንም ወገን አሸናፊነት ማረጋገጥ ተገቢ ይሆናል።
ስድስት ወራት ብቻ የቀሩት ምርጫ 2012 ባልተንዛዛ ሒደት ግልጽ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ ቢጠናቀቅ የአገራችን የፖለቲካ ረፎርም ዋናው አካል ተሳካ ማለት ይሆናል። ምርጫው በጊዜ ሰሌዳው መካሄዱ ተገቢ ቢሆንም የሁሉ ነገር መሠረት የሆነው ሰላም አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ግን ፓርቲዎችም፣ መንግሥትም፣ የዴሞክራሲ ተቋማትም፣ ሕዝቡም አስቀድመው ሊረባረቡባቸው የሚገቡ የቤት ሥራዎች አሉ።
አገር በማስተዳደር ላይ ያለው አካል በየቦታው የሚታዩ ግጭቶችና አለመግባባቶችን በዝምታ ከማለፍ ወይም በኃይል እርምጃ ከመፍታት ይልቅ ሁሉን አቀፍ በሆነ ውይይት የመፍታት ባህል እንዲዳብር አበክሮ መሥራት አለበት። የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫን አሸንፎ ሥልጣን ለመያዝ ከመሯሯጥ በፊት ነገ ወንበር ሲይዙ የሚያስተዳድሯት አገር የተረጋጋችና ሰላማዊ ሆና እንደምትጠብቃቸው እርግጠኛ መሆን ይገባቸዋል። ሰላም የሰፈነበት፣ ዴሞክራሲና ያልታቀበ ተሳትፎ የገነነበት ምርጫ 2012 እውን እንዲሆን ሁሉም ከስሜታዊነትና ከግብታዊነት ወጥቶ መሬት የሚቆነጥጥ ሐሳብ ማፍለቅና ውይይትም ድርድርም ማድረግ ግድ ይለዋል።
ያለመግባባትን በውይይትና በሐሳብ ፍጭት መፍታት ከዚያም ለአሸናፊው ሐሳብ ክብር መስጠት ጊዜው የሚጠይቀው ጉዳይ ነው። ከእልህና ከቂም የጸዳ ፖለቲካ ማራመድ የሠለጠነ ዘመን ፖለቲከኛ መለኪያ ነው። በቀደሙ ሁነቶች ላይ ተማምኖና ያለፈ ታሪክን በታሪክነት ዘግቶ መጪውን ጊዜ በጋራ ለመሥራት መነሳት ያስፈልጋል። በበዳይና በተበዳይ ትርክት ውስጥ ሆኖ በአንድ ምርጫ የጋራ አዲስ ዘመን መገንባት አይቻልም። የነገዋ አገር ሰላም፣ ዴሞክራሲና ዕድገት እውን እንዲሆን ቀዳሚው መፍትሔ ብሔራዊ እርቅና ይቅርታ ነው። ለዚህ ሒደት ግብዓቱ ጽንፈኝነትና ተቸካይነት ሳይሆን ሰጥቶ በመቀበል ላይ ያተኮረ የጋራ ውይይትና ንግግር ነው። ችግርን በጠረጴዛ ዙሪያ የመፍታት ባህልን ማዳበርና “የኔ” ከሚለው ይልቅ “የኛ” የሚለውን ገዢ ሐሳብ ይዞ መጓዝ ለዚህች አገር ሰላም ቀዳሚ መሠረት ነው። በ2012 የምናካሂደው ምርጫ፣ ባላሰብነው መንገድ የግጭት ምንጭ ሆኖ ምርጫ እንዳያሳጣን ከወዲሁ ችግሮችን በውይይት በመፍታት የቤት ሥራችንን ማጠናቀቃችን ለነገ የማያድር የቤት ሥራ መሆን አለበት።