ከተማችን ባልተለመደ ሁኔታ ከበድ ከበድ ያሉ የዝርፊያ ወንጀሎችን ማስተናገድ ከጀመረች ከረምረም ብላለች፡፡ በማህበራዊ ሚዲያም ሆነ በተለያዩ ማስሚዲያዎች ስለዘረፋዎች ዘገባ መስማት ቀጥለናል፡፡ ዜናው ሲበዛ የጀብድ ወሬ የምንሰማ እየመሰለን ነው መሠለኝ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረም ነው፡፡ ሠዎች እራሳቸውን ለመከላከል በማይችሉበት ሁኔታ መኪናን ጨምሮ ሉሎች ከፍተኛ ዋጋ ያላቸውን ንብረቶች እንደ ክብሪት ቀፎ መስረቅ ቀላል ሆኗል፡፡ በደቡብ አፍሪካ እና በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ሰምተን ጉድ ያስባሉን የስርቆት አይነቶች ዛሬ የቅርባችን ጉዳት እየሆኑ መጥተዋል፡፡ “ኬንያ ውስጥ ወርቅ መሸጫ መደብሮች ወርቅ ፊትለፊት ደርድረው አይሸጡም” እያሉ ሲነግሩን፤ እኛስ ፈጣሪ የባረካት ሀገር እንዳለን እየገለጽን እንዲህ ያለው ጉዳይ አያውቀንም ብለን የተመፃደቅን ህዝቦች ዛሬ ምን ገባብን እያልን ነው፡፡ መኪናን በቀላል መንገድ የሚያካብት ባይኖርም በቀላሉ እየተዘረፈ ይገኛል፡፡ ግና የአዘራረፍ መንገድን መስማት እንዴት ያሉ ዘዴኞች ናቸው እንድንል ካልሆነ ጥቅሙ አልታይ እያለን ነው፡፡ዘገባዎችም ቢሆኑ ተዘረፈና እንዴት ተዘረፈ እንጂ ዘራፊዎች ተያዙ ንብረቱም ተገኘኝ አያሠሙንም፡፡ ይህን ያህል የአደባባይ ዘረፋ መቆጣጠር ያቃተን ለምን ይሆን? የሚለው ጥያቄ እንዳለ ሆኖ፤ መድረሻቸው የት ነው? ወንጀልን ለመከላከል ስልጣን እና ኃላፊነት የተሰጠው አካል እንኳን ጉዳዩን የሚመለከተው አካል ይመልከተው በማለት ያለፈው ይመስላል፡፡ ይህን ስናይ ይህች ሀገር ‹‹የሚመለከተው አካል›› የሚባል ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ሳያስፈልጋት አይቀርም ያስብላል፡፡
በሀገሪቱ ወይም በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ጥናትና ምርምር፤ ባለሙያና ገንዘብ ሳያስፈልጋቸው እንዲሁ የሚታዩና የሚታወቁ ችግሮችና የነዚሁ ችግሮች መፍትሔዎች የትየለሌ ናቸው፡፡በህገወጥነት በአንድ ጫፍ የሚያሳድዱት በአንድ በኩል ወደው የሚስሙት ወዳጅ እየሆነ ነው፡፡በአንድ እጃችን ህገወጥ ነው ብለን የተፀየፍነውን ነገር በሌላኛው እጃችን በህጋዊነት ለመቀበል ግድ የማይሠጠን ሆነናል፡፡ ተዘረፍኩኝ ብሎ ሲነግረን ያፅናናንው ወዳጃችንን ንብረት አካል ለኛ ንብረት ጉድለት መሙያ አድርገነዋል፡፡ የስርቆትን ነገር ለመጠቆም ወደ ፖሊስ ጎራ ሲባል ከከንፈር መጠጣው በኋላ የሚለገስዎት ምክርም ንበረቱን ተበትኖም ይሁን በተለየ መንገድ የት እንደሚያገኙት ነው፡፡ ይህንን ለማለት የሚያነሳሳው ደግሞ መንግስት ፈቅዶ ያበጃቸው የሚመስሉ የዝርፊያ መዳረሻዎች ናቸው፡፡ የተሠረቀ ንብረት ገዢ ወይም ተቀባይ ከሌለው ሊበረታታ አይችልም፡፡ ታዲያ መዲናችንም ሆነች ሌሎች ከተሞች ብዙ ህገወጥ ድርጊቶችን የሚረከቡ እና ወደ ህጋዊነት የሚለውጡ በግልፅ የታወቁ ሥፍራዎች አሏት፡፡
ለምሳሌ የኮንትሮባንድ ንግድን እንመልከት፡፡ በሀገሪቱ የኮንትሮባንድ ንግድ የሚከናወንባቸው የድንበር እና መካከለኛ ከተሞች የታወቁ ናቸው፡፡ እነዚህ ከተሞች ለኮንትሮባንድ መንገድ መሆን ብቻም ሳይሆን ኮንትሮባንድን ተቀብለው በህጋዊነት የመሸጥ ልምድ አላቸው፡፡ የኮንትሮባንድ ንግዱ ሥልትና መንገድም እንዲሁ ለዘመናት ሳይለዋወጥ የቆየ መሆኑ አልፎ አልፎ ከሚሰሙ የመያዝ ዜናዎች እና በሥራው ከተሠማሩ አካላት የምናደምጠው ነው፡፡ የእርምጃውና ትኩረቱ መጠን ግን ኮንትሮባንድ ህገወጥነቱ መንገድ ላይ ሲገኝ ብቻ እንደሆነ ያስመስላል፡፡ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ተጉዘው ግልፅ የሆኑ ማረፊያ ሥፍራዎች አሏቸው፡፡ እነዚህ የማረፊያ ከተሞችም ዋነኛ መተዳደሪያቸውን በኮንትሮባንድ በገቡ ዕቃዎች ንግድ ላይ ነው፡፡ ከፍተኛ የሚባል ገንዘብም ይንቀሳቀሳል፡፡ ከሁሉ የሚገርመው በአውራ ጎዳና፤ በመኪና፣ በግመል፣ በአህያ አልያም በሠው ሲዘዋወሩ ቢገኙ ወንጀልነታቸው ከባድ ነው፡፡ ተሽሎክሉከው ከተማ ማረፊያቸው ሲደርሱ ግን ደረሰኝ የሚቆረጥላቸው ህጋዊ ዕቃዎች ይሆናሉ፡፡ መንግስት በአንድ በኩል እያሳደደ በሌላ መንገድ ግብር እያስከፈለበት ከሆነ ማሳደዱ ቀርቶ ቢፈቀድስ የሚል የማበረታታት ስሜትን ይፈጥራል፡፡
ሌላኛውን ግልፅ እውነታ እንመልከት፡፡ የተሰረቀም ይሁን የተጠቀሙት ወርቅ መሸጥ ቢፈልጉ ቀላል ነው፡፡ በዋና ከተማችን እንኳ ዋነኛ መገበያያ ሥፍራ ይታወቃል፡፡ በፒያሳ አለፍ ካሉ የወርቅ ሽያጭ ጋባዥ ወጣቶች ጋር መገናኘቱ ቀላል ነው፡፡ ማጅራት መቺው ቢበረክት ወርቅ መንታፊው ቢበዛ መድረሻ ስላለው ነው፡፡ ኋላማ ወርቅ ዘርፎ አንጥረኛ ሊሆንበት አይደለም፡፡ታዲያ በሀገሪቱ የወርቅ ዝውውር እና ንግድ ሚመራበት የራሱ የሆነ ሥርዐት እንዳለው ይታወቃል፡፡ ሀገሪቱ ካሏት ማዕድናት ውስጥ ቀዳሚው በመሆኑም የሀገር ሀብት እንዳይባክን የመቆጣጠር ስልጣንና ኃላፊነት ያለው አካል ግብይቱን ይመራል፡፡ ከውጭም መጣ ከሀገር ውስጥ ከግለሠቦች፤ የሚዘረፉ ወርቆች መድረሻና ሽያጫቸው በግልፅ ሜዳ ነው፡፡ አሁን አሁን ወርቅ ተመነተፍኩኝ ብሎ ለፖሊስ መጠቆምም እየቀረ የመጣ ባህል ይመስላል፡፡ እንኳንስ ትንሽዬዋ ወርቅ ግዙፍነት ያላቸው እነ መኪና ተዘርፈው እንደ እፉዬ ገላ ሲተኑ ማየት ተለምዷል፡፡
ሌላው ግልፅ የሆነ ህገወጥነት ደግሞ የጥቁር ገበያ የውጭ ምንዛሬ ነው ፡፡ ይኸ ህገወጥ ሥራ ትላንትም ነበረ፣ ዛሬም አለ፣ ወደ ፊትም ይቀጥላል ብሎ በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ከዋናው የሀገሪቱ ገንዘብ ተቆጣጣሪ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ጋር ትከሻ ለትከሻ ተደጋግፈው በውጭ ምንዛሪ ሥራ ከብሔራዊ ትያትር እስከ ጋነዲ መታሰቢያ ሀስፒታል ድረስ ተሰማርተው በመሸጥ የሚተዳደሩ በርካታ ወጣቶች ይገኛሉ፡፡ ይኸ ተግባር ለበርካታ ዓመታት ሲፈፀም የኖረ ነው፡፡ ሕገወጥ ስራውን በግልጽ ሲያከናውኑ የብሔራዊ ባንክ ህጋዊ ወኪሎቹ የሆኑ ይመስላሉ፡፡ ፡ ምንዛሪውን ከባንኩ የሚያቀርቡ ጭምር ይመስላል፡፡ ፖሊስ ኮሚሽኑ በእርምጃ ርቀት የሚገኝ ቢሆንም ምን እንደሚጠብቅ አይታወቅም፡፡በለውጡ ማግስት ማግስት ዘመቻ መወጣቱን ሠማን፡፡ እልል አስባለን፡፡ በቀጥታ ጉዳቱ ቢመለከተነም ባይመለከተንም ህግ ማስከበር የሚለውን ሀሳብ ግን እንለማመደዋለን፡፡ እናም አቀባባይ አሻሻጭ እና መሰል የተባሉ የብሔራዊ አካባቢ ብዙም ያልተሰወሩ ሱቆች ተዘጉ ግለሠቦች ታሠሩ፡፡ ነገር ግን በድርጊቱ ተደስተን ሳናበቃ መንገድ ቀይረው ወረድ ብለው በድላችን ሀውልት ፊት ቆመው “የውጭ ምንዛሬ ይፈልጋሉ?” የሚሉ ወጣቶችን ስናይ የመንግስትን ስነልቦና ህገወጦች ቀድመው እንደሚያውቁት ያስረዳል፡፡ምክንያቱም እርምጃው ያንድ ሠሞን እንጂ የእለት ተእለት ድርጊት እንዳልሆነ እርግጠኞች ናቸውና፡፡ እነዚህ አካላት ምንም አይመጣም በሚል በከፍተኛ እምነት ስራውቸውን ቀጥለዋል፡፡ የህግ አስከባሪዎች እርምጃ እንደ በራሪ ኮከብ በዘመናት መካከል ቆይቶ የሚከሠት ድርጊት በመሆኑ ለህገወጦች መንፈላሰሻ ሆንን፡፡ የብሔራዊ አካባቢ የታወቀ ሥፍራን አነሳን እንጂ በመጠጥ ማከፋፈያዎች እና የጌጣጌጥ መሸጫዎች ውስጥ ተመሳሳይ ግብይይቶች ቀድሞውንም አልተነኩም፡፡ እነዚህ የጥቁር ገበያ ምንዛሬዎች ዋነኛ ተጠቃሚዎች ህጋዊ ነጋዴዎች ናቸው፡፡ ነጋዴ ሁሉ አስመጪ መሆን አለበት የተባለባት ሀገር ይመስል ሁሉም የውጭ ምንዛሬ ፈላጊ በመሆኑ እና በቀላሉ በህጋዊ መንገድ አይገኝም በሚል ሽፋን በህጋዊ መንገድ ሲጠፋ በጥቁር (ህገወጥ) መግዛት ግልፅ እውነታ ነው፡፡ ሚገርመው ነገር በጥቁር ገበያ የተገኝው የውጭ ገንዘብ ለህጋዊ ነጋዴ ተሸጦ ሲሸመትበት እና ሥራ ላይ ሲውል ህጋዊ መሆኑነው፡፡
በዋናነት መጠቆም የፈለኩት ነውና ስለጀመርኩበት ጉዳይ ላንሳ፡፡አዲስ አበባ ላይ መንግስት ለሥራ ፈጠራ ይሁን ለዘረፋ መበረታት ለተሠረቁ ንብረቶች ቦታ መድቦ የሠጠ እስኪመስል ደረስ የታወቁ የዝርፊያ ውጤቶች መሸጫ ቦታዎች አሉ፡፡ መኪና ሲነሳ የብዙዎች አእምሮ ወዴት እንደሚሔድ ግልፅ ነው፡፡ በተለምዶ ሶማሌ ተራ ተብሎ ወደ ሚጠራው ሥፍራ፡፡ በተለምዶ ማለቱ ለምዶብኝ እንጂ አዲስ አበባ ውስጥ የኮነዶሚኒየም ንግድ ቤቶችን በመከራየት የተስረቁ ተሽከርካሪዎች መበለቻና መሸጫ ሆንዋለ. ለደታ ኮንዶሚኒመን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ሶማሌ ተራ ከጥንት ሊባል በሚችል ደረጃ ሥፍራው ወዶም ይሁን ተገዶ የተገነጣጠለ የመኪና አካል ይሸጥበታል፡፡ እንዲያውም ይመረትበታል ማለት ይቀላል፡፡ ምክንያቱም ከነነብሳቸው የገቡ መኪኖችን ወደ አነስተኛ እና ጥቃቅን በመለወጥ ይታወቃሉ፡፡ ታረዱ ይባላሉ፡፡ ከብት ብቻ ሲታረድ የሚያውቅ ሠው መኪና ታረደ ቢባል አንገቱ የቱ ጋ ነው ማን ባረከው የሚል ይመስለኛል፡፡ እና ይህ ሥፍራ ተሠርቀው የቀረቡለትን ዕቃዎች በደረሰኝም ያለደረሰኝም እንደፍላጎትዎ ያቀርባል፡፡ ደረሰኝ የህገወጥነት መከለያ ሽፋን ሆኗል፡፡ የትምፍጪው ዱቄቱን አምጭው አይነት አቋም በመንግስት በኩል ይታያል፡፡ ሥሩ ህገወጥ መሆኑ የአደባባይ ሚስጢር እንደሆነ እየታወቀ በአካባቢው አላፊ አግዳሚውን የሚሸጥ ነው? የሚገዛ አለ እያሉ የሚጠይቁ ወጣቶችን አይቶ እንዳላየ ማለፍን መርጠናል፡፡ ዛሬ ዛሬ መኪና ጠፋብኝ ብሎ ለፖሊስ ሲጠቁሙ የሚያተርፉት ስለሌሎች የተዘረፉ መኪኖች ዜና መስማትን ነው፡፡ ንብረት ሲዘረፍ መያዝ ወይም መከታተል ካልተቻለ ከመድረሻው መነሳት ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡
እየበረከተ የመጣውን አግቶም ይሁን አጭበርብሮ የሚደረግ የመኪና ዝርፊያ መድረሻውን ለመጠየቅ ቢያንስ አንድ ትልቅ እና ግልፅ ቦታ እንዳለን እናውቃለን፡፡ ፖሊስ ይህንን ያህል የምርመራ አቅም ጉድለት አለበት ብዬ ለማመን ቢቸግረኝም ሪፖርት ተቀበሎ እናጣራለን ማለት ልማድ ሆኗል፡፡ ችግርን መላመድ ኢትዮጵያዊ ባህላችን ቢሆንም መንቃት መጀመር አለብን፡፡ ተቀባይ ባይኖር ዘራፊው መኪና ሰርቆ በቀጥታ ለማሽከርከር እንደማያውለው መገመት ቀላል ነው፡፡ በእርግጥ ቀለም እና ሠሌዳ ቀይረው ሲያሽከረክሩ የተገኙ ቢኖሩም በተጎጂዎች ጥረት እንጂ በፖሊስ ስለመሆኑ አልሰማንም፡፡ ፖሊስ በከተማዋ ወንጀል ቀንሷል የሚል ሪፖርት በየመገናኛ ብዙሀኑ ያሰማናል፡፡ በሌላ በኩል መኪናን እና መሠል ስርቆቶች የእለት ተዕለት ቅርብ ወሬዎቻችን ሆነዋል፡፡ ፖሊስ አሁንም እንደድሮው ህዝቡ በሚቀርብለት የቁጥር ሪፖርት አምኖ ንብረቱ እየተዘረፈ ከቀን ወደ ቀን ስጋት ውስጥ እየወደቀ እውነት ነው ብሎ ይቀበላል ብሎ ካሰበ የዋህ ነው፡፡ የፖሊስ ቁጥር የተጠቆመውን እንጂ በመሬት ላይ ያለውን ሊያሳይ አይችልም፡፡ ሠዎች በህግ አስፈፃሚው አካል ያላቸው እምነት እየሳሳ በሔደ ቁጥር መጠቆሙንም እየተዉት መጥተዋል፡፡ መኪና ዘረፉ ጉዳይ ሁላችንንም ሊያሳስበን ይገባል፡፡ ቀላል የማይባል የግለሠብ ብቻ ሳይሆን የሀገርም ገንዘብ አብሮ እንደሚዘረፍ ሊሰማን ይገባል፡፡
እዚህች ሀገር ላይ ከመሬት ቀጥሎ ትልቅ ገንዘብ የሚፈስበት ንብረት ቢኖር መኪና መሆኑ እሙን ነው፡፡ ከመነሻው ካቃተን ከመድረሻው ለመነሳት መድፈር አለብን፡፡ ውጤት የማንሰማ ከሆነ ሥጋታችን እየጨመረ አዳዲስ ሌቦችን እየፈጠርን መሔዳችን አይቀሬ ነው፡፡ ሶማሌ ተራን እንደመነሻ አነሳን እንጂ በመኪና ዝርፊያ ውስጥ ብዙ ተባባሪ አካላት አሉ፡፡ ከነነብሳቸው ተዘርፈው በኩራት የተዘረፉ መኪኖችን ሠሌዳ በመቀየር እና ህጋዊ ሊብሬ እንዲይዙ በማድረጉ ውስጥ የመንገድ ትራንስፖርት ሠራተኖች እጅ እንዳለበት ግልጽ ነው፡፡ ከኢንሹራንስ የሚገኙ በጉዳት የተያዙ መኪኖችን ሠሌዳ እና የሻንሲ ቁጥር መጠቀም የታወቀ ድርጊት ሆኗል፡፡ እነዚህን ከመሠረቱ ከኢንሹራንስ ከመሸጣቸው በፊት የሚሰረዙበትን መንገድ ማማቻቸት አንድ ነገር ነበር፡፡ ይህ ባለመሆኑ ለሚሠረቁ መኪኖች ህጋዊ ሽፋን አግኝተው እንደልብ እንዲንቀሳቀሱ መንገድ ሆነዋል፡፡ በነገራችን ላይ ከኢንሹራንስ በጉዳት ምክንያት የተያዙ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ የኖረ የታወቀ ጠቀሜታ አላቸው፡፡ መሐል ከተማ በጨረታ ተገዝተው ሻንሲያቸው እና ሠሌዳቸው በኮንትሮባንድ ለሚገቡ ተሽከርካሪዎች ሽፋን ሲሆኑ ኖረዋል፡፡ ይህ ሁሉ እውነታ ከፖሊስ የተደበቀ ነው ለማለት ይቸግራል፡፡ የሌባን አሠራር ከፖሊስ በላይ የሚያውቀው የለም፡፡ አውቆ የተኛን ቢጠሩትም ቢጠረጥሩትም አይሰማም አይነት ሆኖ ነው እንጂ፡፡ በትናንሽ የመኪና አካላት ተጀምረው ዛሬ ከነነብሱ መኪናውን በመዝረፍ የተማረርንበት ከተማ ትላንት በትንንሹ እቃችንን መልሰን ለመግዛት የሄድንባቸው ሥፍራዎች ዛሬም መኪኖቻችንን ተረክበው ስለመበለታቸው እና ስለመቀየራቸው አንጠራጠርም፡፡ ነገር ግን ሪፖርት ከመቀበል በላይ ምንም ሲያደርግ የማናየው ፖሊስ ከግለሠብ በላይ አቅም እና ኃላፊነት እያለው ደፍሮ ለመፈተሽ እና ለመመርመር የወደደ አይመስልም፡፡ በቅርብ ርቀት እያየን ዝም ያልናቸው ችግሮች አይን አፍጠው የራሱ የፖሊስን ንብረት እስከመዝረፍ ደርሰዋል፡፡ ደግነቱ የነሱ ሲሆን ተያዘ ሲባል ይሰማል፡፡ ምስኪኖቹስ ማን አለሁ ይበላቸው፡፡ ወይስ የእድገት መለኪያችን ተምታቶብን ከአንዳንድ በዝርፊያና ውንብድና ከሚታወቁ ሀገራት ጎን ስማችንን ለማስጠራት እየጣርን ነው፡፡ ሠርተን አላልፍልን ቢል የሌብነት እድገት ይቅርብን፡፡ ሌብነት የወጣቶቻችን መገለጫ እየሆነ ከመምጣቱም በላይ በህብረተሰባችን ውስጥ አለመተማመን በከፍተኛ ሁኔታ ሠፍኗል፡፡ ምንጩን መያዝ ካቃተን ከመድረሻው ወይም ከመንገዱ ለመያዝ መቻል አለብን፡፡ ስለመኪና ስርቆት በዋናነት የሚመለከተው የታወቀ ስፍራ ሶማሌ ተራ ቢሆንም የተለያዩ የመኪና መለዋወጫ መሸጫ ቤቶችም ከእነዚህ እቃዎች ይይዛል እንጂ ጦሙን እንደማያድር የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡ ከዘራፊው ተረካቢው ከዛም መልሶ ገዢው ሞልቷል፡፡ዘራፊ የት እንደሚያደርሰው እና ምን እንደሚያደርገው ቀድሞ ያውቃል፡፡እኛው ተዘራፊ እኛው ተረካቢ እኛው ሻጭ እኛው ገዢ ነን፡፡ ሠሚ የሌለው ጩኸት እየሆነ እሪ በከንቱ የአንድ ሠፈር መጠሪያ ሳይሆን የሀገር መጠሪያ ሊሆን ደርሷል፡፡ ተቀባዩም ቢሆን ኃላፊነት እንዳለበትና ተጠያቂ መሆን እንዳለበት ሊያምን ይገባል፡፡ ተሰርቆ እስከመጣ ድረስ እኔ ምን ቸገረኝ ከደሙ ንፁህ ነኝ አካሔድ የትም አያደርስም፡፡ በሐሞራቢ ዘመን ቢሆን ኖሮ የተዘረፈ ባለመኪና የተረካቢዎችን መኪና መልሶ በመውሰድ ህመሙን ማሳየት ይቻል ነበር፡፡መኪናንም ሆነ ከላይ ለአብነት የተነሱ የስረቆት መዳረሻዎች ሳይታወቁ ቀርተው ሳይሆን በይሁንታ መተዋቸውን እናስተውላለን፡፡ በሀገሪቱ እውነት ህገወጥነትን ለመከላከል እንፈልጋለን ወይ የሚል ጥያቄን የሚያስነሱ ነጥቦች ናቸው፡፡ በግልፅ ያሉ ድርጊቶችን መንግስትም ለመቆጣጠር የሚያሳየውን ቸልተኝነት ሲታይ ሆን ብሎ ትቷቸዋል የሚያስብል ነው፡፡ እነዚህ ህገወጥ ድርጊቶች በውስጠ ታዋቂነት ኑሮን ያመጣጥናሉ ብሎ ያሰባቸውም ይመስላሉ፡፡ ምንዛሪውን በበቂ ሁኔታ ማቅረብ ባለመቻሉ፣ ወጣቱ ሥራ ሥላጣ፣ የመኪና መለዋወጫ እንዳይጎድለን፣ በርካሽ ዕቃዎችን እንድንገዛ እየታሰበልን ታይቶ እንዳልታየ የሚታለፉ ድርጊቶች አስመስሎታል፡፡ ህገወጥነት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው አካል በመሆኑ መንግስትም ከትርፉ ተቋዳሽ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት ተዘርፎ የተገኘን ንብረት በደረሰኝ ቫት አስከፍሎ የሚሸጥ ነጋዴ እያለ መቼም ለመንግስት ከትርፉ አልደረሰውም ለማለት አይቻልም፡፡ መኪና ዕቃ ጎድሎት ለመጠየቅ ወደ እነዚህ ሱቆች ጎራ ሲሉ ነገ እፈልግልሀለሁ ይባላሉ፡፡ ነገ አሠርቅልሀለሁ ማለት እንደሆነ ከአንዳንድ ተጠቃሚዎች የምንሰማው ነው፡፡ነገር ግን ወሬያችን እና ትኩረታችን ሁሉ ድርጊቱ ላይ ብቻ እየሆነ መድረሻቸውን እየረሳነው ነው፡፡ ተቀባዩ ከሌለ ዘራፊው የት ይደርሳል፡፡ ሽፋን ሰጪ ተባባሪ ከሌለ መዝረፍ ዋጋ ያጣ ነበር፡፡ ግልፅ እና የታወቁ የህገወጦች መገበያያዎች ላይ ህግ አስከባሪው ሊያተኩር ይገባል፡፡ እርምጃዎችም የቀን ተቀን ሥራ እንጂ የአንድ ሰሞን ሞቅታ መሆን የለባቸውም፡፡ ሌባ ተቀባይም ያው ሌባ ነው የሚል አባባል በማህበረሰባችን የኖረ አባባል ቢሆንም አሁን ላይ ተሽሯል፡፡ የንግድ ፈቃድ አውጥተው ቤት ተከራይተው በግዢም በስርቆትም የቀረበላቸውን ዕቃ የሚሸጡ ነጋዴዎች እጅ ግብር በመሰብሰብ መንግስትንም እጁን እንዲያስገባ እየተደረገ ነው፡፡ የህግ አስከባሪው አሠራር እና ፍጥነት ከህገወጡ መቅደም ባይችል መጠጋት መቻል አለበት፡፡ አሁን ላይ የምናየው ግን የመኪና ዝርፊያውም ሆነ ሌላው ድርጊት ከህግ አስከባሪው የመቆጣጠር አቅም በላይ ነው፡፡ የተለመዱ የምርመራ አሠራሮችን እንኳ ተከትሎ የተዘረፉት ንብረቶች የት ሊደርሱ ይችላሉ የሚለውን ለመከተል እስቲ ወደ እነዚህ ሠፈሮች ጎራ በሉ፡፡ እናንተም እኛም እኩል ፈርተናቸው መቀጠል ይከብዳል፡፡ ዓለም ከአመድ እና ከአጥንት ውስጥ ማስረጃ ፈልፍሎ አውጥቶ ወንጀለኛን ለፍርድ የሚያቀርብበት ዘመን ላይ ደርሰን ንብረታችንን በጠራራ ፀሀይ ተዘርፈን እምጥ ይግቡ ስምጥ አልታወቀም እንባላለን፡፡ እምጡም ስምጡም በቅርባችን ናቸው፡፡ ሳንሰምጥ ተጠግተን ለመፈተሽ አልወደድንም እንጂ ተበትነውም ይሁን ከነህይወታቸው ንብረቶችን ለማግኘት የሚያስችሉንን መንገዶችን መፍጠር እንችላለን፡፡ የአንድና የሁለት ሠዎችን ንብረት ፈልፍለን ለማግኘት ጥረት ባለማድረጋችን የመቶዎች ችግር እየሆነ መጥቷል፡፡ በዚህ ከቀጠልን አንዳችን የሌላኛችንን መኪና ገዝተን መንገድ ላይ ስንተላለፍ እየተፋፈርን እንዳንሳሳቅ፡፡ ያው በታወቀው የመላመድ አባዜያችን ሚሊዮን እና ብዙ ሺህ ብሮችን አፍስሰን የገዛናቸውን ንብረቶች ማጣትን እንላመድ ብንል እንኳ መቋቋም አንችልም፡፡ እናም ወገኖች ተዘረፍን እና ተሰረቁ ዜና ማወጁ ብቻውን መፍትሔ አይሆንም፡፡ ፖሊስም የቁጥር ሪፖርቱን ገታ አድርጎ እውነት ችግሩ የት ጋ ነው ብሎ ሀይሉን አሠባስቦ ወደ እርምጃ ሊገባ ይገባል፡፡ የተለመደ ቢሮ ተቀምጦ ማስረጃን ተጎጂ እንዲያቀርብ የመፈለግ ልማድ ሊቀር ይገባል፡፡ ተጎጂ ማስረጃን መሰብሰብ አቅም እና ችሎታ ካለው ፖሊስም አቃቤ ህግም እርፍ ይሉ ነበር፡፡ ነገር ግን በህግ ሥርዐት እመራሉሁ በምትል ሀገር እየኖርን ፖሊስ ሥራውን በትክክል ካልሠራ የሌቦች መናኸሪያ መሆናችን አይቀርም፡፡ ወጣ ብሎ መረጃንም ማስረጃንም የማሰባሰብ ስራን መለማመድ ያስፈልጋል፡፡ መኪና ተዘረፍኩኝ ብሎ ለሚጠቁም ተበዳይ ምስክር አለህ ብሎ ቀድሞ መፍትሔ እንደሌለው የሚያመላክት ምላሽ መስጠት ምን ጥቅም አለው፡፡ ምስክር አቁሞ የሚዘርፍ ሌባ አልሰማንም፡፡ ወጣ ብሎ የተዘረፉ ንብረቶች የት እንደሚደርሱ በሚታወቁባቸው ስፍራዎች መፈተሽ አንዱ አማራጭ ነው፡፡ የወንጀል ትንሽ እና ትልቅ የለውም፡፡ ሌባን ብቻ ሳይሆን ተቀባይንም እያበረታታን ወንጀልን በጋራ እንከላከል የሚል መፈክር ብቻውን መፍትሔ አይሆንም፡፡ የሌባ ተቀባይን እኩል ትኩረት ካልሰጠነው ስርቆትን ለመያዝ የሚደረገው ጥረት ፍሬ አልባ ይሆናል፡፡ በመሆኑም ተቀባይን ማትፋት ሌባን ማጥፋት ነውና ሁሉም ተባብሮ መስራት አለበት እላለሁ፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊዋ ጠበቃና የሕግ አማካሪ ሲሆኑ ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡ ፀሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው[email protected] ማግኘት ይችላሉ፡፡