ሰሞኑን በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች በኦሮሚያ ክልል የታገቱ ሴት ተማሪዎችን አስመልክቶ በተካሄደ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የተሳተፉ አንድ እናት ለሚዲያ በሰጡት አስተያየት፤ “ስለልጆች የማይገደው መንግስት አባት አይባልም !” ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
በብዙ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ “መንግስት አባት ነው” የሚል የከረመ አባባል አለ። “መጠጊያ ያጡ ዜጎችን የሚሰበስብ፣የተበደሉትን የሚክስ፣ ለምንዱባን ጥብቅና የሚቆም፣ ያለቀሱትን እምባ የሚያብስ፣ የተከሰሱን ይቅር የሚል …ሁሉን አስተዳዳሪ ፣ የሁሉ መከታ ነው” የሚሉትን መንግስት፤ ዜጎች እንዲህ የአባትነት ሚና ይቸሩታል ። ምናልባትም ከመንግስት ባህሪ ህልዮቶች ውስጥ አንደኛው በሆነው አባታዊ መንግስት ( patriarchal state) ውስጥ በሚመደበው የንጉሳዊ አስተዳደር ውስጥ ስላለፍንም ይሆናል ‘መንግስት አባት ነው’ የሚለው አሳብ የሰረጸብን። የሆነው ሆኖ በዘመናዊው የመንግስት አረዳድ ውስጥም ቢሆን መንግስትና ፓርቲ በተለያዩበት ስርዓት ከብዙ በጥቂቱም ቢሆን አንድ መንግስት ከላይ የተዘረዘሩት ባህሪያት ይኖሩታል። የመንግስት ቀዳሚ ውግንና ለተበደሉ እና ድምጽ ላጡት ነው። ምንዱባንና ተራ ዜጎች ከፈጣሪ ቀጥሎ ተስፋ የሚያደርጉበት አንድ የበላይ አካል ካለ መንግስት ብቻ ነውና “መንግስት አባት ነው” ቢሉ መሰረት አላቸው።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግስት ህግን የማስከበር አቅሙ የተዳከመ መስሎ መታየቱ ብቻ ሳይሆን በተግባርም መዳከሙ መረጋገጡ በሃገሪቱ ስርዓተ አልበኝነት እንዲነግስና በዜጎች ላይም የሰላም ስጋት እንዲያድር ምክንያት ሆኗል። በውጤቱም መንግስት አባት ነው በሚሉትም ዘንድ ቢሆን የመንግስት “አባትነት” ጥያቄ ውስጥ ገብቷል። ከሁለት ወር በፊት ማንነታቸው በማይታወቅ አጋቾች እጅ የወደቁትና መኖር አለመኖራቸውን በርግጠኝነት ለመናገር እንኳን በቂ መረጃ ያልተገኘላቸውን ሴት ተማሪዎች ጉዳይ ስናስብ ደግሞ በርግጥም መንግስት የአስተዳዳሪነቱንና የጠባቂነቱን “አባታዊ” እሴቶች ሙሉ በሙሉ ማጣቱን ያሳየናል። ለዚህም ነው ወይዘሮዋ አንዳሉት ህዝቡ “ልጆቼን ሊጠብቅልኝ ያልቻለውን መንግስት አባት ብዬ አልጠራውም” የሚለው።
ለአብዛኛው በድህነት ወለል ስር ለሚኖር ኢትዮጵያዊ ፣ በተለይም አፈር ገፍቶ ጉሮሮውን ለመዝጋት ለሚታትር ገበሬ፤ ልጅ ማለት ተስፋ ማለት ነው። ብዙው ኢትዮጵያዊ ልጅ ወልዶ የሚያሳድገው በተፈጥሮ ህግ ዘሩን ለማስቀጠል ብቻ አይደለም ። በእርጅና ዘመኑ ጧሪ ፣በድካሙ ጊዜም ቀባሪ እንዳያጣ ሲል እንጂ። ከነብሂሉም “ጧሪ ቀባሪ ያድርግህ” ብሎ ልጅን የሚመርቀው ይህንኑ ለማጉላት ነው። ተቸግሮ ያስተማረ፣ ከጥሪቱ ቆንጥሮ ሳይሆን ጥሪቱን አሟጦ ልጁን ዩኒቨርሲቲ የላከ ወላጅ የቀን ከቀን ተስፋው ሳይማር ያስተማራቸው ልጆቹ ደርሰው እርሱ ካለበት ድህነት እንዲያላቅቁት ነው። በተለይ ሴት ልጆቹን ስንት ባህላዊ ሽሙጥ እና ወጋዊ ክልከላዎችን ጥሶ ያስተማረ ወላጅ ፣ አስተምሮም ለዩኒቨርሲቲ ያበቃና ተስፋውን በነርሱ ላይ ያንጠለጠለ ደሃ ወላጅ መንግስት ባለበት ሃገር ልጆቹ ባልታወቁ አጋቾች እጅ ወድቀው ለሁለት ወር ድምጻቸው ሳይሰማ ሲቀርበት ሞተዋል ከመባል ያልተናነሰ ሃዘን ጭኖበታል። የሰቀቀን ሌሊት እየገፋ ከመኖር ያለፈ ጉልበት አጥቶ አሁንም ተስፋውን በመንግስት ላይ አንጠልጥሏል።
የዶክተር ዐቢይ አስተዳደር ሊወነጨፍ ጥቂት የቀረው በመሰለ የጎጥ ፖለቲካ ባላ ፊት ቆሞ ራሱንም ፣ ህዝቡንም ከወንጭፉ ማትረፍ የተሳነው መስሏል። አንዲት ሉዓላዊት ሃገርና ህዝቧን እንደሚያስተዳድር መንግስት ሲታይ የአሁኑ መንግስት ዜጎቹን መጠበቅ እና ሰላም ማስከበር ያልቻለ የደካማ መንግስት ባህሪ ተላብሷል። ባለፉት 18 ወራት ካሳለፍነው ህግና ስርዓት አልባነት በላይም የአሁኑ የሴት ተማሪዎች እገታ የመንግስት አቅም አልባነት ገንኖ የታየበት ሆኗል። የአስተዳደሩ የደህንነት መዋቅርና የወንጀል መከላከል አቅም ጥያቄ ውስጥ ብቻ ሳይሆን ተስፋ የማይጣልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ ነው። በነዚህ ታጋች ልጆች የተነሳ የመንግስት የሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ ብቃት በብዙ ማጋደል ውስጥ እንዳለ በህዝብ እየተገመገመ ነው።
የሴት ተማሪዎቹ እገታ ጉደይ ሲነሳ በመንግስት ላይ ያሉት ሁለት ዋና ዋና ችግሮች ጎልተው ይወጣሉ። አንዱ በሚመራው ሃገር ውስጥ ሊያሸንፈው ያልቻለ ስርዓትና ህግ አልባ ቡድን መኖሩን ሲያሳይ ሁለተኛው ደግሞ መዋቅሩ የህዝብን የማወቅ መብት ማክበር የማይችል አሰራር ማስፈኑን ነው። የፖለቲካ አለመረጋጋት ባለበትና የዘር ቁርቋሶ በገነነበት በዚህ ጊዜ የነዚህ ሴት ልጆች መታገት የችግሩ አንድ ነጸብራቅ ቢሆን እንጂ የሚያስገርም ነገር አይደለም። ነገር ግን መንግስት በበቂ ጥንቃቄ እና ሃይል ታጋቾቹን የማስለቀቅ ሃላፊነት የርሱ ብቻ ነው። በዚህ ሂደት ውስጥ ደግሞ መረጃን ለህዝብ መግለጽ እና ስጋትና መላ ምቶችን ማረጋጋት ተጨማሪ ሃላፊነቱ ነው።
መንግስት የሁለቱንም ሂደት መረጃ ለታጋቾቹ ወላጆች እና ለህዝቡ በበቂ መጠን መግለጽ አለመቻሉ ፣ የሚሰጣቸው መረጃዎችም የተበጣጠሱና የተምታቱ መሆናቸው ህዝቡን አስቆጥቷል። ለዓለም አቀፍ መብጠልጠልም ዳርጎታል። ህዝብ በመንግስት ላይ ያለውን ዕምነት እንዲሸረሸር እና በአስተዳደሩ ላይም ተስፋ እንዲቆርጥ አድርጎታል።
የዶክተር ዐቢይ መንግስት እንደፌዴራል መንግስት በሚያስተዳድረውና በጂኦግራፊያዊ ክልሉ ውስጥ በሚገኝ ማናቸውም ስፍራ ላይ በቂ የቁጥጥር ሃይል እንደሌለው ያሳየው ይህ እገታ ሃገሪቱ በሁለት መንግስታት የምትተዳደር አስመስሏታል። በነዚህ ታጋቾች ጉዳይ እስካሁን ሃላፊነት የወሰደ አካል ባይኖርም ከመንግስት ባለስልጣናት አፍ የሚወጡ መረጃዎችና የሚሰጡ መግለጫዎች ግን አንዴ “ከአጋቾቹ ጋር ድርድር እየተደረገ ነው” የሚሉ ሌላ ጊዜ ደግሞ “አጋቾቹን ለማወቅ ጥረት እየተደረገ ነው” የሚል እርስ በርሱ የሚቃረን እየሆነ ህዝቡን ግራ እያጋባ ነው። በሌላ በኩል “ታጋቾቹ ተለቅቀው ወደዩኒቨርሲቲያቸው ተመልሰዋል” ሲባል በሌላ ጊዜ ደግሞ “ተማሪዎቹ ለፖለቲካ ጥቅም ሲሉ ራሳቸውን ሰውረው እንደሆነ በሚል ጉዳዩ እየተጣራ ነው” የሚል ሃላፊነት የጎደለው መግለጫም ከመንግስት ሃላፊዎች እየተሰማ ነው። በሰላም ሚኒስትሯ የተመራው ቡድን በደንቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ያደረገው ቆይታም ሆነ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ባለስልጣናት ከታጋች ወላጆች ጋር ባደረጉት ስብሰባም አንዳቸውም አፍ ሞልቶ ለመናገር የሚያስችል መረጃ አልወጣቸውም።
“እምነት እንደሸክላ ነው፣ አንዴ ከተሰበረ ዳግም ለመጠገን ይቸግራል” እንዲሉ በተለያዩ የሃገሪቱ አካባቢዎች ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን አስተያየቶች በመነሳት ህዝብ በመንግስት ላይ ያለውን የዕምነት ተስፋ ለማሟጠጥ የቀረው ርቀት ይህ የታጋቾች የመጨረሻን ማወቅ ብቻ መስሏል። መንግስት የህዝብን የማወቅ መብት ማክበርና መረጃውን በተገቢው ደረጃ ማሳወቅ ግዴታው ነው። የአጋች ታጋች ጉዳይን መፍታት ከፍ ያለ ጥንቃቄና ምስጢራዊ ተግባር የሚፈልግ መሆኑ እሙን ቢሆንም ቢቻል በየወቅቱ በጉዳዩ ላይ መንግስት የደረሰበትን ደረጃ በተገቢው መንገድ ማወቅ ለሚገባቸው አካላት መግለጽም ይጠበቅበታል። አጋቾቹ እነማን ናቸው? ልጆቹን ለምን አገቷቸው? ታጋቾቹ በምን ሁኔታ ላይ ናቸው? ለማስለቀቅ መንግስት ምን እየሰራ ነው? የሚሉትና የመሳሰሉት ወሳኝ መረጃዎች በፍጥነት ለህዝብ መድረስም ይገባቸዋል። ይህን ካላደረገ “አለሁ” የሚለው መንግስት “በተግባር የለም” ተብሎ ህዝብ የመጨረሻ ቅጣቱን በካርድ ሊያደርገው እንደሚችል ሊያስጠነቅቀው ይገባል። ብዙዎች እንደሚሉት አሁን ስልጣን ላይ ላለው የዶክተር አብይ ፓርቲ ይህ ጉዳይ ነጥብ የሚጥልበት ወሳኝ ጉዳዩ ነው። ከዚህ አጣብቂኝ ለመውጣት ምን እንደሚያደርግ ደግሞ ጊዜ የሚያሳየን ይሆናል።በኛ በኩል ግን የአጋች ታጋች ድራማው ሽፋን እስኪገለጥ እና ሁኔታዎች በቁጥጥር ስር እስኪውሉ ድረስም ቢሆን እውነተኛ፣ የታጋች ወላጆችንና ህዝቡን ማረጋጋት የሚያስችል እና የተደራጀ መረጃ የሚሰጥበትን ቋሚ መንገድ ማመቻቸት ይገባዋል እንላለን። የአንድ መንግስት ቀዳሚ እሴቱ ለሚመራው ህዘብ ታማኝ እና ተጠያቂ መሆኑን በተግባር ማረጋገጡ ነውና።