ኦሊምፒክ የዓለምን ኅብረተሰብ በአንድ መድረክ በማሰባሰብ ከስፖርታዊ ማዕከልነት እስከ ባህላዊ ትዕይንት በማገናኘት ወደር ያልተገኘለት፣ አቻ ያልተፈጠረለት እውነተኛ መንፈስ ነው ይሉታል፡፡ ዘመናዊ ኦሊምፒክ በግሪክ መዲና አቴንስ ከተጀመረ ዘንድሮ 124ኛ ዓመት ላይ ደርሷል፡፡ 32ኛውን ኦሊምፒያድን ከአምስት ወራት በኋላ የምታስተናግደው የጃፓን መዲና ቶኪዮ ናት፡፡ ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች በመጪው ሐምሌ ለሚካሄደው ግዙፉ የዓለም የስፖርት ማገናኛ መድረክ በብቃት ለመሳተፍ የተጠናከረ ዝግጅት እያደረጉ ነው፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ኦሊምፒኩን የሚመራው ኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ (ኢንኦኮ) ኦሊምፒክ የቆመባቸውን መርሆዎች ለማስጠበቅ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ የኦሊምፒክ መንፈስ ከማናቸውም የፖለቲካ ሆነ የኢኮኖሚ ተቋማት እንዲሁም ከመንግሥታት ተፅዕኖ ውጭ በሆነ ተቋም የሚመራ ቢሆንም በየዐረፍተ ዘመኑ ፈተናዎች ማጋጠማቸው አልቀረም፡፡
ከማናቸውም ዓይነት ተፅዕኖዎች ነፃ በሆነ መንገድ የኦሊምፒኩን እንቅስቃሴ ብቸኛው ድርጅት ኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ (ኢንኦኮ) እንዲመራ ፈረንሳዊው ባሮን ደ ኩበርቲን በዘመናዊ መልኩ ሲፈጥሩት ለጨዋታዎቹ ዕድገት ለፕሮግራሞቹ ሥምረት እንዲበጅ አድርገው ነው፡፡
ነገር ግን በየወቅቱ ስፖርት በተለያዩ መደቦች ልዩ ልዩ አመለካከትን በማግኘቱ በዓለም ላይ ታዋቂ፣ በሕዝብ ዘንድ ተደናቂ የሆነው ኦሊምፒክን ለመደባቸው በቆሙ ኃያላን መንግሥታት ስፖርቱን ምክንያት በማድረግ ልዩ የፖለቲካ ውጤት መድረክ ለማድረግ ሞክረዋል፣ አድርገውታልም፡፡
ያም ራሳቸውን ከተዘጋጁት የኦሊምፒክ ውድድሮች በማግለል ከተሳትፎ መቅረት ሲሆን ለዚህም ምክንያት በመደርደር በዓለም ላይ ልዩ የፖለቲካ ትኩረትን በማግኘት የዓላማ ግባቸውን ለማሟላት ሲሞክሩ ታይተዋል፡፡
የኦሊምፒክ አቋም በጽኑዕ መሠረት ላይ በመቆም እስከ 1980 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. 1988) ይከሰቱ በነበሩት ፖለቲካዊ ግጭቶች ምክንያት የማቋረጥ ሁኔታ በሴዑል 24ኛው ኦሊምፒያድ 96% የቀረ ሲሆን፣ የተለያዩ ርዕዮት ያላቸው አገሮች ኃያላኑን ጨምሮ ከማሳተፍ ደርሷል፡፡ ቀዝቃዛው ጦርነት አብቅቶ፣ የምዕራብ ምሥራቅ ፍጥጫ ቀርቶ ሁሉም በኦሊምፒክ ጥላ ሥር በአንድነት ሲያሳትፍ ቆይቷል፡፡
ይሁን እንጂ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሌላ መልክ የያዘው የኦሊምፒክ መድረኩን በልዩ ልዩ ምልክቶች የፖለቲካ ማንፀባረቂያ፣ የተቃውሞ መግለጫ የሚያደርጉ አትሌቶች መታየት ጀምረዋል፡፡
ባለፈው ነሐሴ በሊማ ፔሩ በተካሄደው የፓን አሜሪካ ጨዋታዎች በሻሞላ ወርቅ ያገኘው አሜሪካዊው ሬስ ኢምቦዴን የአገሩ ብሔራዊ መዝሙር ሲዘመር በሽልማት ሠገነቱ ላይ መቆም ሲገባው፣ በርከክ ብሎ እጁን ጉልበቱ ላይ በማስቀመጡ የአሜሪካ ኦሊምፒክና ፓራሊምፒክ ኮሚቴ የአንድ ዓመት ዕግድ ጥሎበታል፡፡

ሌሊሳ ፈይሳ በተቃውሞ ምልክት
ፎቶ ስፖርትስ ፕሮ
ይህ ጉዳይ በብርቱ ያሳሰበው ዓለም አቀፉ የኦሊምፒክ አካል በቅርቡ አዲስ ድንጋጌ አውጥቷል፡፡ ፖለቲካዊ መልዕክት ያላቸው የእጅና የጉልበት ምልክቶች፣ በሜዳሊያ ሽልማት ሥነ ሥርዓት ላይ ክብርን የሚፃረር ተግባር መፈጸም በጥብቅ የተከለከለ መሆኑን ኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴ (ኢንኦኮ) አስጠንቅቋል፡፡
በኦሊምፒክ ቻርተር አንቀጽ 50፣ አትሌቶች ተቃውሞ ከማሳየት እንዲቆጠቡ ቢከለክልም እስካሁን ምን ዓይነት ተቋውሞ እንደሆነ ግልጽ ያለ ነገር አልነበረውም፡፡ አዲሱ መምርያ ግን አትሌቶች ስሜታቸውን በጋዜጣዊ መግለጫዎችና በማኅበራዊ ሚዲያ ማንፀባረቅ እንጂ በስፖርቱ ሜዳ ወይም በይፋ የሽልማት ሥነ ሥርዓቶች ላይ መፈጸም የተከለከለ ነው፡፡ በማሳያነት የቀረቡት የተከለከሉ የተቃውሞ ዓይነቶች በርከክ ማለትን ጨምሮ “ፖለቲካዊ ቅኝት” ያላቸው የእጅ ምልክቶች፣ መልዕክቶችን በምልክት ወይም እጅን በማመሳቀል ማሳየትና በማንኛውም የሽልማት ሥነ ሥርዓቱን ማወክ ናቸው፡፡ ድንጋጌውን የሚሱ አትሌቶች በየደረጃው የዲሲፕሊን ርምጃ ይወሰድባቸዋል፡፡
ኢንኦኮ እንዳስታወቀው፣ መመሪያው የተዘጋጀው ኦሊምፒክና ስፖርት በአጠቃላይ ከፖለቲካ የራቁ መሆን አለባቸው በሚለው እሳቤ ነው፡፡ “ስፖርት ገለልተኛና ከፖለቲካ፣ ከሃይማኖት ወይም ከሌሎች ጣልቃ ገብ ነገሮች የተለየ መሆኑ መሠረታዊ መርሆ ነው፤”ሲልም አክሏል፡፡
ኢንኦኮ በኦሊምፒክ ቻርተር ድንጋጌ 50 መሠረት ያዘጋጀው መመርያ (ጋይድ ላይን) በ2020 ቶኪዮ ኦሊምፒክ አትሌቶች ሕግና ሥርዓትን ማክበር እንደሚገባቸው ጠቁሞ በመወዳደሪያ ቦታዎች፣ በኦሊምፒክ መንደር፣ በሜዳለያ ሽልማትና በሌሎች ሥነ ሥርዓቶች አንዳች ዓይነት የተቃውሞ ምልክት ማሳየት አይፈቀድም፡፡ ይህን ጥሶ የተገኘ ማንኛውም አትሌት ይታገዳል ብሏል፡፡ የኦሊምፒክን መንደርና የሽልማቱን ሠገነት ከማንኛውም የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም የጎሳ እንቅስቃሴ ነፃ ማድረግ ያስፈልጋልም ሲል ያስገነዝባል፡፡
አዲሱን ድንጋጌ ተከትሎ አትሌቶች ድምፃቸውን እንዳያሰሙ ለምን ይደረጋል ብለው የጠየቁም አልታጡም፡፡ የኢንኦኮ አባልና የአትሌቶች ኮሚሽን ሊቀመንበሯ ክርስቲ ኮቬንትሪ “ማብራሪያ እንሻለን፣ በሕጎቹም ዙርያ እንዲሁ ማብራሪያ ይፈልጋሉ፣ አብዛኞቹ አትሌቶች እንደ አትሌት መከባበር በጣም አስፈላጊ መሆኑን ያምናሉ፤” ማለቷ ኤፒ ዘግቧል፡፡
እንደ የኢንኦኮ ፕሬዚዳንት ቶማስ ባህ አገላለጽ፣ ኦሊምፒክ “የፖለቲካና የከፋፋይነት አጀንዳ ማራመጃ መደላድል አይደለም”፡፡
በኦሊምፒክ የተፈጠሩ ክስተቶች
የዘመናዊ ኦሊምፒክ ጨዋታ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ፖለቲካ በስፖርት ላይ መጫወት ጀምሯል፡፡ ከ1870-71 በተከናወነው ጦርነት ፈረንሳይ በጀርመን መረታቷ መራር ትዝታን በመቅረፁ ከጀርመን ጋር መወዳደራቸው አሳስቦ ነበር፡፡ ቢሆንም በፒየር ባሮን ደ ኩበርቲን ከፍተኛ ጥረት ፈረንሳይ ያላትን ቅዋሜና ቅሬታ እንድታነሳ በማድረግ በ1ኛው ኦሊምፒያድ ሁለቱም እንዲካፈሉ ተደርጓል፡፡
እ.ኤ.አ. በ1906፡ የአየርላንድ ነፃነት
በዘመናዊ ኦሊምፒክ የመጀመርያ ተቃውሞ ተብሎ የተሰነደው የአየርላንድ አትሌት ፒተር ኮነር በእንግሊዝ ስም አልወዳደርም ማለቱ ነው፡፡ በርዝመት ዝላይ የብር ሜዳሊያን ካሸነፈ በኋላ ከእንግሊዝ ባንዲራ አጠገብ ይቆማል ተብሎ ሲጠበቅ የአይሪሽን ባንዲራ ከሰንደቁ ላይ አውለብልቧል፡፡
1956፡ የሶቪየት ወረራ
16ኛው ኦሊምፒያድ በሜልቦርን፣ አውስትራሊያ ሲካሄድ ኔዘርላንድስና ስፔን የሐንጋሪ በሶቭየት ኅብረት መወረር ምክንያት አንካፈልም በማለት ወጡ፡፡ ስዊዘርላንድ ሶቪየትን በመቃወም ላለመካፈል በመጀመሪያ የወሰነች ቢሆንም ቃሏን በማጠፍ ተሳተፈች፡፡
1964–1988: የአፓርታይድ ዘመኑ ደቡብ አፍሪካ ዕገዳ
በዘመናዊ ኦሊምፒክ የመጀመሪያዎቹ ሃምሳ ዓመታት ውስጥ ጎልቶ የታየው ችግር የፈረንሳይና የጀርመን ጠብ እንዲሁም ሁለቱ የዓለም ጦርነቶች ሲሆን በጥቁር ዘር በተለይም በአፍሪካውያንና በዘረኛው የደቡብ አፍሪካ ሮዴዢያ መካከል የተደረገው ከኦሊምፒክና ከስፖርት ዓለም ለማግለል የተደረገው ፍልሚያ እልህ አስጨራሽ ነበር፡፡
ደቡብ አፍሪካ በሚከተለው ዘርአዊ የአፓርታይድ ሥርዓት ምክንያት እንዲታገድ የአፍሪካ አገሮች በኢትዮጵያዊው የኢንኦኮ አባል አቶ ይድነቃቸው ተሰማ አስተባባሪነት በመጠየቃቸውና በኦሊምፒክ ጨዋታዎችም ላለመካፈል በተደጋጋሚ መወሰናቸው ተከትሎ ከሁለት አሠርታት በላይ ታግዶ ቆይቷል፡፡ የአፓርታይድ ሥርዓት እ.ኤ.አ. በ1991 ከተወገደ በኋላ የደቡብ አፍሪካ ተሳትፎ ቀጥሏል፡፡
1968: የጥቁር ኃይል
በጣም ታዋቂ ከሆኑት የኦሊምፒክ ምስሎች አንዱ በሜክሲኮ ኦሊምፒክ ባለሜዳሊያ የሆኑት አፍሪካ አሜሪካውያኑ የአጭር ርቀት ሯጮች ቶሚ ስሚዝና ጆን ካርሎስ፣ በሽልማት ሠገነት ላይ ሆነው ጥቁር ጓንት ያጠለቀውን እጃቸውን ከፍ አድርገው የአገራቸውን ባንዲራና ብሔራዊ መዝሙር በማቅለል ‹‹የጥቁር ኃይል›› መንፈስን በኦሊምፒክ መድረክ ያሳዩበት ነበር፡፡ ይህም ከኦሊምፒክ ቻርተርና ሥነ ምግባር ውጪ የፈጸሙት ድርጊት እንደሆነ ተቆጥሯል፡፡
1976፡ አፍሪካውያን ያልተካፈሉበት
ከታገደችው ደቡብ አፍሪካ ራግቢ ቡድን ጋር ኒውዝላንድ በመጫወቷ፣ ሞንትሪያል ካዘጋጀችው 21ኛው ኦሊምፒያድ መታገድ አለባት በሚል አብዛኞቹ የአፍሪካ አገሮች ሳይካፈሉ ቀርተዋል፡፡
1980 እና 1984: ቀዝቃዛው ጦርነትና ያለመካፈል አቋም
አገሮች በኦሊምፒክ ያለመካፈል አቋም ከወሰዱባቸው ሰባት ኦሊምፒኮች መካከል ጎልቶ የሚታወቀው የምሥራቅና የምዕራብ ጎራዎች በሞስኮና ሎስ አንጀለስ ጨዋታዎች ላለመካፈል መወሰናቸው ነበር፡፡
የሶቪየት ኅብረት መንግሥት አፍጋኒስታንን በ1979 በመውረሩ ምክንያት አገሪቱን ለቆ ካልወጣ በስተቀር በ22ኛው ኦሊምፒያድ ሞስኮ ላይ የኦሊምፒክ ቡድኖቻችንን አንልክም በማለት በአሜሪካ አስተባባሪነት ከ60 የማይበልጡ አገሮች እንደማይካፈሉ ገለጹ፡፡ ተግባራዊም አደረጉት፡፡
23ኛው ኦሊምፒያድም የአሜሪካ ከተማ በሆነችው በሎስ አንጀለስ ሲዘጋጅም ሶቭየት ኅብረትና ሌሎች ሶሻሊስት አገሮች ኢትዮጵያን ጨምሮ በቁጥር 17 ለአትሌቶቻችን ደህንነት ያሰጋናል በማለት ከኦሊምፒኩ ውድድር ቀሩ፡፡ የ140 አገሮች ብሔራዊ ኦሊምፒክ ቡድኖችም ተሳታፊ ሆኑ፡፡ ሁለቱ ተከታታይ ኦሊምፒያዶች የኃያላኑ አገሮች መተያያና መበቃቀያ መድረክ አድርገውት አልፏል፡፡ በእነዚሁ ጨዋታዎች ለኦሊምፒክ መንፈስ ክብር በመስጠት ለሁለቱ ኃያላን መንግሥታት ተቀጽላ አንሆነም በማለት በ1980 ሞስኮ ላይ እንግሊዝና ፈረንሳይ ሲገኙ በ1984 ሎስ አንጀለስ ላይ ሩማኒያና ዩጐዝላቪያ ተገኝተዋል፡፡
1988፡ ሰሜን ኮርያ
የኦሊምፒክ ጨዋታን ከሦስተኛው ዓለም ሀገሮች በማስተናገድ ረገድ የላቲን አሜሪካዋ ሜክሲኮ ቀዳሚዋ አገር ስትሆን፣ ሁለተኛዋ አገር (1988) በመሆንም ሩቅ ምሥራቅ እስያ የምትገኘዋ ደቡብ ኮሪያ ተመዝግባለች፡፡ ከተማዋ ሴዑል 24ኛውን ኦሊምፒያድ ስታስተናግድ የምሥራቁም ምዕራቡም ጎራ በአንድነት የታየበት ነበር፡፡ ደቡብ ኮርያ ኦሊምፒኩን የማዘጋጀት ዕድል በ1981 ሲሰጣት ጠበኛዋ ሰሜን ኮሪያ በፀጋ አልተቀበለችም፡፡ የኢንኦኮ ውሳኔ ተለውጦ የኦሊምፒኩ ጨዋታ በኅብረት ለማዘጋጀት እንዲፈቀድ ብትጠይቅም አልሆነላትም፡፡ ሰሜን ኮርያ በእኔም ካልተዘጋጀ ብላ አልካፈልም ስትል ኩባና ኢትዮጵያ ባለመካፈል ተቀላቅለዋታል፡፡
ሰሜን ኮርያ በ23ኛው ኦሊምፒያድ የሶቭየት ደጋፊ ሆና ከሎስ አንጀለስ እንደቀረች ሁሉ እኩል በእኩል 24ኛው ኦሊምፒያድ ለማዘጋጀት ዕድል ካልተሰጣት ሶሻሊስት አገሮችንና ሦስተኛ ዓለም አገሮች ተባብረዋት እንዲቀሩ ለሦስት ዓመታት ብትጥርም አልተሳካላትም፡፡ በጥረቷም ወቅት ኮሚኒስት አገሮች ጨዋታዎቹን በሁለቱ ኮርያዎች እንዲካሄድም ጠይቀዋል፡፡ እንደዚህ ያለ መጠይቅ ሲነሳ በኦሊምፒክ ታሪክ የመጀመሪያው ነው የምዕራብ ጀርመን ከተማ ሙኒክ 20ኛው ኦሊምፒያድ በ1972 ስታዘጋጅ ከምሥራቅ ጀርመን ጋር አብረው እንዲያዘጋጁ ኮሚኒስት አገሮች አልጠየቁም ነበር፡፡
2004: ኢራናዊ ከእስራኤል ጋር አልጋጠምም ማለቱ
በአቴንስ በተከናወነው የ2004 ኦሊምፒክ ኢራናዊው የዓለም ጁዶ ሻምፒዮኑ አራሽ ሚርሴማሊ ከእስራኤላዊው ኢሁድ ቫካስ ጋር አልጋጠምም ያለው እስራኤል “በፍልስጤም ላይ ችግር አድርሳለች” በማለት ነው፡፡
2008: የቲቤት ደጋፊዎች ሰልፍ
ቻይና በቲቤት ላይ ያላትን አያያዝ በመቃወም ወደ አዘጋጇ ከተማ ቤጂንግ የኦሊምፒክ ችቦ ከመድረሱ በፊት በሚዘዋወርባቸው አህጉሮች ትዕይንተ ሕዝብ ተካሂዷል፡፡
2014: የተመሳሳይ ጾታ አራማጅ ቀለሞች
በሩሲያ ሶቺ ኦሊምፒክ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ አራማጅ አትሌቶች የቀስተ ደመና ቀለሞችን በአካላቸውና በልብሶቻቸው ላይ በማድረግ መታየት ጀመረ፡፡
2016: የሌሊሳ ፈይሳ ተቃውሞ
ኢትዮጵያ በሪዮ ኦሊምፒክ በማራቶን በሌሊሳ ፈይሳ አማካይነት የብር ሜዳሊያ ያገኘችበት ነበር፡፡ ይህም ድል በወንዶች ማራቶን ለመጨረሻ ጊዜ በ2000 ሲድኒ ኦሊምፒክ ገዛኸኝ አበራና ተስፋዬ ቶላ ወርቅና ነሐስ ካገኙ በኋላ የተገኘ ነው፡፡ ሌሊሳ ከኬንያዊው ኢሉድ ኪፕቾጌ ቀጥሎ ሁለተኛ ሆኖ ያጠናቀቀው በወቅቱ በኢትዮጵያ የነበረውን የመንግሥት ሥርዓት መቃወሙን እጁን በማመሳቀል አሳይቷል፡፡
2020: ቶኪዮ ኦሊምፒክ
የዘንድሮው የቶኪዮ ኦሊምፒክ ከሐምሌ 27 እስከ ነሐሴ 3 ቀን 2012 ዓ.ም. የሚካሄድ ሲሆን፣ የዓለም ፀረ ዶፒንግ ድርጅት (ዋዱ) አትሌቶቿ በዶፒንግ ተጠቃሚነታቸው ሳቢያ በቶኪዮ 2020 በጋ ኦሊምፒክና በቤጂንግ 2022 ክረምት ኦሊምፒክ እንዳትሳተፍ ሩሲያን አግዳቷል፡፡
የቶኪዮ ኦሊምፒክን አትሌቶች በሽልማቱ ሠገነት ላይ በዝምታ ያልፉታል ወይስ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ድምፅን ያስተጋቡበት ይሆን?