ከግማሽ ትሪሊዮን ብር በላይ የሚፈልገው
የግንባታ ኢንዱስትሪ
የኢትዮጵያ የግንባታ ኢንዱስትሪ ብዙ ይባልለታል፡፡ ኢንዱስትሪው የአገሪቱን 60 በመቶ በላይ በጀት የሚቀራመት ግዙፍ መስክ ነው፡፡ በዚህ ኢንዱስትሪ መሠረተልማት፣ የከተማ ልማት፣ የገጠር ልማት፣ የህንጻ ወይም የመኖሪያ ቤቶች ግንባታና ሌሎችም ሥራዎች ይሸናሉ፡፡ ይሁን እንጂ የኢንዱስትሪውን ግዙፍነት ያህል የሚመጥኑ መገለጫዎች አይታዩበትም፡፡
ዘርፉ በአብዛኛው በመንግሥት ግዥ የሚከናወኑ ሥራዎች የሚበዙበት፣ በቴክኖሎጂ ረገድ እንደሚታበውና እንደሚጠበቀው ብዙ ያልተራመደ፣ ይልቁንም ከውጭ በሚገቡ ማሽነሪዎችና ጥሬ ዕቃዎች ላይ ጥገኛ የሆነ ግዙፍ ዘርፍ ነው፡፡ አብዛኛው የግንባታ ሥራም በማኑዋል ወይም በሰዎች ትከሻ ላይ በተንጠለጠለ ሥርዓት የሚመራ በመሆኑ፣ ለከባድ ሙስና፣ ለፕሮጀክቶች መጓተት፣ ለተጋነነ ወጪና ለዋጋ ንረት የተጋለጠ ሆኖ ቆይቷል፡፡
ለዚህ ማሳያው በመንግሥት ያለ በቂ ጥናትና አቅም የተጀመሩ ትልልቅ የስኳር ልማት ፕሮጀክቶች፣ የኃይል ማመንጫዎች፣ ትልልቅ የመስኖ ግድቦች፣ የባቡር ፕሮጀክቶችና የሰፋፊ እርሻ ሥራዎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ መንግሥት እንዲህ ያሉትን ፕሮጀክቶች ለማካሄድ ከአገር ውስጥና ከውጭ ምንጮች ከፍተኛ ገንዘብ በመደበር በጀት ሲመድብ ቆይቷል፡፡ አገሪቱ በአሁኑ ወቅት ከአገር ውስጥና ከውጭ የተበደረችው የገንዘብ ዕዳ መጠን ከ1.6 ትሪሊዮን በላይ ይገመታል፡፡ ከዚህ ውስጥ አብዛኛው ለግንባታ ሥራዎች እንዲውል ተፈልጎ የተከማቸ ዕዳ ሆኖ ይገኛል፡፡
በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር አማካይነት ተሰናድቶ በቅርቡ ለውይይት የቀረበው የ10 ዓመታት የግንባታ ኢንዱስትሪው ዓብይ ዕቅድ ረቂቅ፣ ከመጪው ዓመት ጀምሮ እየታሰበ እስከ 2022 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ የሚዘልቅ የ10 ዓመታት የዘርፉን ክንውኖች ይፋ አድርጓል፡፡ በዚህ ዕቅድ መሠረት የግንባታ ኢንዱስትሪ በጠቅላላው ከ650 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ያስፈልገዋል፡፡ ይህን ያህል ገንዘብ የሚጠይቁት የሥራ መስኮችም የከተማ ፕላንና መሬት ዘርፍ፣ የቤት ልማት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ ብድር አቅርቦት፣ የምግብ ዋስትና ፕሮጀክት፣ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ፣ ለተለያዩ የግንባታ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ፣ ለአቅም ግንባታ፣ ለተቀናጀ የመሠረተልማት ዘርፍ፣ ለፅዳት አገልግሎትና አረንጓዴ ልማት ሥራዎች ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አብላጫውን ገንዘብ የሚፈልጉት ሥራዎች ደግሞ የተቀናጀ የመሠረተ ልማት ዘርፍ ዋናው ነው፡፡
በአሥር ዓመታት ውስጥ ከ250 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚያስፈልገው ሰነዱ አስፍሯል፡፡ የተቀናጀ የመሠረተልማት ሥራ በአብዛኛው በመንገድ፣ በውኃ፣ በመብራትና በቴሌኮም መስክ የሚከናወኑ ሥራዎችን አቀናጅቶ የመገንባት አካሄድን የሚከተል ነው፡፡ ከዚህ ዘርፍ በመከተል ትልቁን የበጀት ድርሻ የሚሸፍነው የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪው ነው፡፡ ከ190 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚያስፈልገው ተጠቅሷል፡፡ የሥራ ዕድል ብድር አቅርቦት ከ188 ቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብለት፣ አቅም ግንባታ ከ130 ቢሊዮን በላይ ያስፈልገዋል ተብሏል፡፡
እንዲህ ያሉ ግዙፍ የፋይናንስ ፍላጎቶችን በዓመቱ እያስተናገደ ለመጪዎቹ አሥር ዓመታት፣ ከዚያም አልፎ ለ30 ዓመታት የሚዘልቁ ፍኖተ ካርታዎች እየተዘጋጁለት የሚገኘው የኢትዮጵያ የግንባታ ኢንዱስትሪ በበርካታ ትብታቦች የታጀለና በአሁኑ ወቅት በተለይም የኮንስትራክሽን ኢንዲስትሪው መቀዛቀዝ ውስጥ እንደሚገኝ ይነገራል፡፡ ይህ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ምክንያቶች መካከል የፋይናንስ እጥረት አንዱ ሲሆን፣ የጸጥታ ሥጋትም አብሮ ይነሳል፡፡ ባንኮች የሚሰጡት ብድር በማጣታቸው ምክንያት ለኮንስትራክሽን ሥራዎች የሚውል ገንዘብ እንዳልተገኘ እሮሮ ሲቀርብ ከርሟል፡፡
በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን በተደረገው ውይይት ወቅትም ይኸው የገንዘብ እጥረት ጉዳይ ተነስቷል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ በጠሩት የከተማው ተቋራጮችና ባለሀብቶች ስብሰባ ወቅትም ይህ ችግር አንዱ ማነቆ ስለመሆኑ ተወስቶ ነበር፡፡
ከገንዘብ እጥረት ባሻገር፣ የመሬት አቅርቦት አለመኖር፣ የወሰን ማስከበር ችግሮች፣ የጥሬ ዕቃ አቅርቦት ማጣትና የመሳሰሉት የፕሮጀክቶችን የውል ጊዜ ማጓተትና በተገባው ውል መሠረት አጠናቆ አለማስረከብ በሰፊው የሚታዩ ችግሮች ናቸው፡፡ በዚህ ሳቢያ የዋጋ ንረትን በማስከተልና ከመነሻው የተበጀውን የፕሮጀክት ወጪና የታበሰውን የገንዘብ ሀብት መጠን እጅጉን በማሻቀብ ረገድ በኢትዮጵያ የሚካሄዱ የግንባታ ሥራዎችን የሚስተካከላቸው ያለ አይመስልም፡፡
በ10 ዓመታት ዓብይ የዘርፉ ረቂቅ ሰነድ በተጠቀሰው መሠረት፣ በ2011 ዓ.ም. በፌደራል ደረጃ የተመዘገቡ 2070 ፕሮጀክቶች ይገኛሉ፡፡ የአገር አቀፍ የኮንስትራክሽን ፕሮጀከት አፈጻጸም ነባራዊ ሁኔታን እንደሚያሳዩ የተጠቀሱና የኮንትራት ዋጋቸዉ ከ37 ቢሊዮን ብር በላይ የሆኑ 52 ከፍተኛ የፌደራል መንግሥት ፕሮጀከቶችም በትግበራ ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህም 10 የውኃ፣ 10 የህንፃ ግንባታ፣ 32 የመንገድ ፕሮጀክቶች ሲሆኑ፣ በእነዚህ ፕሮጀክቶች ላይ በተካሄደ የዳሰሳ ጥናት መሠረት የኮንስትራክሽን ፕሮጀክቶቹ 66 በመቶ አማካይ የውል ጊዜ ማራዘም ያስከተሉና 124 በመቶ የጊዜ ጭማሪ የተደረገባቸው፣ በዋጋ ረገድም የ76 በመቶ ጭማሪ ያሳዩ ናቸው፡፡
በዓለም አቀፍ የሚጠቀሰው ምርጥ ተሞክሮ ለጊዜ መራዘም የሚኖረው ጭማሪ ቢበዛ ከዘጠኝ በመቶ የማይበልጥ ሲሆን፣ በዋጋ ረገድ የሚያስከትለው ጭማሪም ከስድስት በመቶ የማይበልጥ ስለመሆኑ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ይህም ይባል እንጂ እንደ ቻይና ያሉ ምጡቅ አገሮች ግን በሁለት ቀናትና በሳምንት ጊዜ ውስጥ አስገራሚ ግንባታዎችን በማካሄድ ዓለምን ጉድ ያሰኛሉ፡፡ ቻይና ባጋጠማት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ በአንድ ጊዜ ከ1000 በላይ የቫይረሱ ተጠቂዎችን አስተኝቶ ለማከም የሚያስችል ግዙፍ ሆስፒታል በሁለት ቀናት ውስጥ ገንብታ ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረጓ ሲታይ፣ በኢትዮጵያ በአንጻሩ ዓመታትን ፈጅተውም የማይጠናቀቁ፣ በሁለት ዓመታት ይገበዳዳሉ የተባሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች 10 ዓመታት ቆይተው ከጅምራቸው ፈቅ የማይሉ ሆነው ይታያሉ፡፡ የመንገድ፣ የውኃ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎች፣ የማዳበሪያና መሰል ፕሮጀክቶች ለመስማት የሚከብድ ከፍተኛ መዋዕለ ነዋይ ፈሶባቸውም ግንባታቸው በተጀመሩበት የቀሩ ናቸው፡፡ እንዲህ ያሉት ፕሮጀክቶች ከአገር ውስጥ የፋይናንስ ምንጮች በተለይም ከኢትዮጵያ ልማት ባንክና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፈሰስ የተደረገው ገንዘብ የኢትዮጵያ ከሁለት ዓመታት አጠቃላይ በጀት በላይ የሚሸፍን ሆኖ ይገኛል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአንድ ዓመት በፊት በገለጹት አኃዝ መሠረት፣ ንግድ ባንክ ብቻውን ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ያበደረው ያልተመለሰ ገንዘብ ከ400 ቢሊዮን ብር በላይ ነው፡፡ ይህም ለ10 ዓመታት ያስፈልጋል ከተባለው የ650 ቢሊዮን ዶላር ግማሽ በላይ መሆኑ ነው፡፡

የመሣሪያና የግብዓት ችግሮች
የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪውን የፋይናንስ ዕጥረት ከሚያባብሱት ችግሮች መካከል የኮንስትራክሽን መሣሪያዎች አቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም አንዱ ነው፡፡ እስካሁን በአማካይ ከ400 ያልበለጠ ማሽነሪ በየዓመቱ እየተመረተ ወይም እየተገጣጠመ ሲቀርብ መቆየቱን የዘርፉ መረጃዎች ያሳያለ፡፡ ሆኖም የተመረቱትን ማሽነሪዎች ወደ ተጠቃሚዎች በማዳረስ በኩል ችግሮች አሉ፡፡ ይህ ባለበት በአማካይ በየዓመቱ እስከ አምስት ሺህ ማሽነሪዎች ከውጪ እየገቡ ይገኛሉ፡፡ በጥቅሉ አገሪቱ ከተጠቀመችው አጠቃላይ ማሽነሪ ውስጥ በአገር ውስጥ የተገጣጠመውና የተመረተው የማሽነሪ ብዛት ከ10 በመቶ በታች ሆኖ ይገኛል፡፡
የአርማታ ብረት አቅርቦት ጉዳይ ቢታይ፣ በ2007 ዓ.ም. በከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር በተደረገ ጥናት መሠረት፣ የአርማታ ብረት አገር ውስጥ ያመርቱ የነበሩ 12 ድርጅቶች በአጠቃላይ የማምረት አቅማቸው 1,240,836 ቶን ቢሆንም፣ በ2006 ዓ.ም ማምረት የቻሉት 274,736 ቶን ነበር፡፡ የኮንስትራክሽን ዘርፉ ከተጠቀመው የአርማታ ብረት አንጻር በአገር ውስጥ የተሸፈነው አቅርቦት 54 በመቶ ብቻ መሆኑ የግብዓት አቅርቦት ችግሩን አጉልቶ ሰነዱ አስፍሯል፡፡
በግንባታ ማጠናቀቂያና በሌሎችም ተጓዳኝ ምርቶች አቅርቦት በኩል ሰፊች ችግር ይታያል፡፡ ለአብነትም በአገር ውስጥ የተመረተው የመፀዳጃና የእጅ መታጠቢያ ሴራሚክ አቅርቦት ከስድስት ዓመታት በፊት 6.9 በመቶ ብቻ ይሸፍን ነበር፡፡ የግድግዳና የወለል ንጣፍም በአገር ውስጥ የሚመረተውና አቅርቦትን መሸፈን የቻለው መጠን ከስድስት በመቶ በታች እንደሆነ የዘርፉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የኬሚካል ኢንድስትሪ መረጃዎች እንደሚያሳዩትም፣ ከ2007 እስከ 2011 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ በሴራሚክ ምርት አገራዊ አቅርቦቱ ላይ ይህ ነው የሚባል ዕድገት አልተመዘገበም፡፡
በአገር ውስጥ ፋብሪካዎች አማካይነት የኤሌክትሪክ ዕቃዎችን የማምረት አቅም ሲታይ፣ 12,871 ቶን ምርት ለማምረት የሚችሉ አቅም ያላቸው ፋብሪካዎች ቢኖሩም፣ ያመረቱት ግን 4‚900 ቶን ገደማ ብቻ ነው፡፡ ይህም ከማምረት አቅማቸው 38 በመቶ ብቻ እንደሚያመርቱ ታውቋል፡፡ ኢትዮጵያ ከሚያስፈልጋትና ከተጠቀመችው አጠቃላይ የኤሌክትሪክ ዕቃዎች ፍላጎት አኳያ በአገር ውስጥ ምርቶች የተሸፈነው 57 በመቶ ብቻ እንደሆነም መረጃዎች አሳይተዋል፡፡ በአገር ውስጥ የሚመረተው መስታወትም ቢሆን፣ በ2007 በተደረገ ጥናት መሠረት አጠቃላይ ከአገሪቱ ፍላጎት 50 በመቶ ብቻ መሸፈን ሊሸፍኑ የሚችል ምርት ቢቀርብምም የቅርብ ጊዜ ጥናቶች ግን በግማሽ ቀንሶ፣ በአሁኑ ወቅት ሊሸፈን የቻለው የምርት መጠን ከአገራዊ ፍላጎት አኳያ 25 በመቶ ብቻ ሆኗል፡፡
እነዚህን መሠረታዊ ችግሮች የሚፈታ መፍትሔ ተግባራዊ ባይደረግም፣ የግንባታ ኢንዲስትሪው ግን ከመጪው ዓመት ጀምሮ በዓመቱ ከ50 ቢሊዮን ብር እስከ 83 ቢሊዮን ብር በሚደርስ በጀት የሚተዳደርበት የ10 ዓመታት ዓብይ ዕቅድ ወይም መሪ ፕላን ተዘጋጅቶለታል፡፡ ከፍተኛ የገንዘብ ሀብት የሚሽከረከርበት በመሆኑም ለከፍተኛ የሙስና ወንጀሎች የተጋጠ ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለዘርፉ ተዋንያን እንደገለጹት፣ በሙስና በሚያገኙት ሀብትና ንብረት ሳቢያ የማይታዘዙ፣ ችግር የሚፈጥሩ ባለሥልጣናት እየተበራከቱ መምጣታቸውን ገልጸው ነበር፡፡ በተለይ ከግዥ ጋር በተያያዘ በሚፈጸሙ በርካታ ማጭበርበሮች ሳቢያ ባለሥልጣናት መታሠራቸው ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ የመንግሥት ባለሥልጣናትንም ሆነ የግንባታ ኩባንያዎችን እንዲህ ካለው የሙስና አዘቅት ሊያወጣቸው የሚችል የግዥ ሥርዓት መከተል እንደሚገባ ከሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ የዩናይትድ ኮንሰልቲንግ ኢንጂነርስ ማኔጂንግ ዲሬክተርና የኢትዮጵያ ሲቪል መሐንዲሶች ማኅበር ፕሬዚዳንት ተስፋዬ ወርቅነህ (ኢንጂነር) ናቸው፡፡
እንደ ተስፋዬ (ኢንጂነር) ማብራሪያ፣ ሙስናን ከኮንስራክሽን ዘርፉ ለማስቀረት አንዱ መንገድ የጅምላ ወይም bulk ግዥ ሥርዓት ነው፡፡ ‹‹የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ላይ የሚታየውን አድልኦ፣ ሽኩቻና መሰል ችግር ለመቅረፍ፣ በኮታ በማደል የዋጋ ንረትን ጭምር ለመከላከል ያስችላል፡፡ የግብዓት ግዥ ላይ ተመሳሳይ ዋጋ ከተቀመጠ የግንባታ ሥራ ላይ የሚቀርበው ክርክር በትርፍና በመሰላሉት ላይ ብቻ ይሆናል፡፡ ሌብነት መቀነስ የሚቻለው በዚህ ዓይነቱ መንገድ ነው፡፡›› ብለው ነበር፡፡ ይህ አሠራር ጥናት ተደርጎበትና ታምኖበት ቢወጣም፣ ሳይተገበር ረጅም ዓመታት ማስቆጠሩን ባለሙያው ገልጸዋል፡፡
ይሁን እንጂ መንግሥት እንዳሰበው ከ10 እስከ 30 ዓመታት ባለው ጊዜ ውስጥ የኢትዮጵያ የግንባታ ኢንዱስትሪ አገሪቱን ከመካከለኛ ኢኮኖሚ ተርታ የማሰለፍ ዓላማ ላይ የተንተራሰ ዕቅድ ሊተገበር ዝግጅት ተጀምሯል፡፡ እነተስዬ (ኢንጂነር) የሚመሩትና ‹‹ኢትዮጵያ፡ 2050›› የተሰኘ ዓለምአቀፍ ጉባዔም በመጪዎቹ 30 ዓመታት ውስጥ የኢትየጵያን ፈታኝ መንገዶች ከወዲሁ ማደላደልና ማስተካከል የሚቻልበትን ጥርጊያ ከወዲሁ ማበጀት ጀምሯል፡፡
መንግሥትም በአዲሱ ዕቅዱ የሥራ ዕድል በሚፈጥሩ የጥቃቅን፣ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ልማት፣ አካታችና ዘላቂነት ያለው የከተማ ፕላንና ልማት፣ አዋጭነት፣ ግልፅነትና ተጠያቂነት ያለበት የመሬት አቅርቦትና ማኔጅመንት፣ ኅብረተሰቡንና የግሉን ዘርፍ ያሳተፈ የቤት ልማትና አቅርቦት፣ በጥራት፣ በተመጣጣኝ ወጪ፣ በወቅቱና በተወዳዳሪነት የሚሠራ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪና የኮንስትራክሽን ማኔጅመንት አሠራር ብሎም የማስፈጸም አቅም የመገንባት ዓላማዎችን የማሳካት ዕቅዶች የተቀመጡት የአገሪቱ የኮንስትራክሽን ልማት፣ ገጠርና ከተሞችን ከማልማት አኳያም ተልዕኮዎች እንዳሉት በሰነዱ አስፍሯል፡፡
ይህ እንዲሆን ግን ሁሉም የአቅሙን ማዋጣት እንዳለበት የሚመክሩት ተስፋዬ (ኢንጂነር)፣ ‹አሁን ያለው መንግሥትም ሆነ ሁላችንም በተበላሹ ሥራዎች ውስጥ እንዳለንና ከዚያ ውስጥ የመውጣት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ይህ ሲሳካም ‹‹ከዚያ ወጥተን በአዲስ መድረክ ላይ ከተገኘን፣ የተሻለች ኢትዮጵያ ትመጣለች፡፡ መንገድ፤ድልድይ፣ ፋብሪካውና ጤና ጣቢያ የሚሠራው ለእኔ ነው የሚል ዜጋ ሲኖረን የተሻለች ኢትዮጵያ፣ የተሻለ የኮንስትራክሽን ዘርፍ ይኖረናል፡፡›› በማለት ምኞታቸውን አስታውቀው ነበር፡፡