የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19)ወረርሽኝ ዓለምን በብዙ መልኩ እየፈተነ አራት ወራትን አስቆጥሯል፡፡ በጤና ላይ ከሚያደርሰው ቀጥተኛ ጉዳት ባለፈ በተለያየ መልኩ የአገሮችን ኢኮኖሚ እያሽመደመ፣ ጠንካራ የሚባሉ አገሮችን ሳይቀር እያመሰቃቀለ፣ ለማሰብ በሚከብድ ፍጥነት ዓለም የምትመራበትን ሥርዓት እየለወጠ ይገኛል፡፡ ቫይረሱ በቀላሉ ከሰው ወደ ሰው መተላለፍ መቻሉ ደግሞ ሥርጭቱን ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡ በርካታ አገሮች ወረርሽኙን ቀድሞ ለመከላከል የተለያዩ ጥረቶች ሲያደርጉ ቢቆዩም የኮሮና ቫይረስ በአጭር ጊዜ ውስጥ በርካታ አገሮችን በማዳረስ ለዓለምን ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ከቷል፡፡
በሽታው የተከሰተባቸው አገሮች የቫይረሱን ሥርጭት ለመግታት የተለያዩ ዕርምጃዎችን እየወሰዱ ሲሆን፣ አብዛኛዎቹ የዓለም አገሮች ትምህርት ቤቶች ሙሉ በሙሉ አሊያም በከፊል እንዲዘጉ ወስነዋል፡፡ ውሳኔውም በዓለም ላይ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ውጭ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የሕጻናት አድን ድርጅት (ዩኒሴፍ) ይህንን ቁጥር 1.6 ቢሊየን እንደሚደርስ ይገልፃል፡፡ ይህን ያህል ቁጥር ያለው ተማሪ ከትምህርት ገበታው ሲናጠብ በዓለም ላይ ይህ የመጀመሪያው ክስተት እንደሆነም ይናገራል፡፡
የኮሮና ቫይረስ በዓለም የትምህርት ሥርዓት ላይ ትልቅ ጉዳት እያደረሰ ይገኛል፡፡ ለቫይረሱ መከላከያ ወይንም መድኃኒት ባለመገኘቱና ሥርጭቱም በፍጥነትና በስፋት እየጨመረ መሄዱ፣ ወረርሽኙ በቁጥጥር ስር የሚውልበትን ጊዜና ሁኔታ ለመገመት አስቸጋሪ ከማድረጉም ባለፈ፣ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው የሚመለሱበትን ጊዜና ሁኔታ ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ አድርጎታል፡፡ አንዳንድ የዓለም አገሮች ለጊዜው የትምህርት ሒደቱን በተወሰነ መልኩ ለማስቀጠል የሚስችሉባቸውን ዘዴዎችን በመጠቀም ትምህርትን በሬዲዮ፣ በቴሌቪዥን፣ በኢንተርኔትና በመሳሰሉት በመታገዝ፣ ተማሪዎች በያሉበት ትምህርት የሚያገኙባቸውን የተለያዩ ጥረቶች እያደረጉ ቢገኙም አገልግሎቱን ማግኘት የሚችሉት በከተማ የሚኖሩና ወይንም የቴክኖሎጂዎቹ ተጠቃሚዎች ብቻ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ፣ ከተደራሽነት አንጻር ሁሉንም ተማሪዎች መድረስ ባለመቻሉ የፍትሐዊነት ጥያቄ ያስነሳል፡፡ አስነስቷልም፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ የኮሮና ቫይረስ የመግባቱ ዜና ይፋ መደረጉን ተከትሎ ከመጋቢት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ትምህርት ቤቶች ለተከታይ አሥራ አምስት ቀናት እንደሚዘጉ መንግሥት ውሳኔ ያስተላለፈ ቢሆንም፣ የወረርሽኙ አሳሳቢነት እየጨመረ በመምጣቱ፣ ትምህርት ቤቶች ሁኔታዎች መሻሻል እስኪያሳዩ ድረስ ተዘግተው እንዲቆዩ ተደርጓል፡፡ በአሁኑ ወቅት በተፈጠረው ሥጋት ምክንያት በአገሪቱ በሁሉም ዕርከኖች ላይ በሚገኙ ትምህርት ቤቶችና የከፍተኛ ተቋማት ውስጥ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ ከ32 ሚሊየን በላይ ተማሪዎች ከትምህርት ውጭ መሆናቸውን የትምህርት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል፡፡ ወረርሽኙ በኢትዮጵያ አጠቃላይ የትምህርት ሥርዓት ላይ እያደረሰ ስላለውና ሊያደርስ ስለሚችለው አጠቃላይ ጉዳት ለመናገር የቫይረሱን የሥርጭትና የጉዳት መጠን ማወቅ ግድ ቢሆንም ወረርሽኙ በሥርጭትና ሽፋን እየጨመረ እንዲሁም የወረርሽኙ ጊዜ እየረዘመ ከሄደ፣ በትምህርት ሥርዓቱ ላይ የሚኖረው ጉዳትም እየከፋ እንደሚሄድ መገመት ቀላል ነው፡፡
ማዕረጉ ቢያበይን (ዶ/ር) በኮተቤ ሜትሮፖሊታንት ዩኒቨርሲቲ፡ በትምህርት አመራርና አስተዳደር ረዳት ፕሮፌሰር ናቸው፡፡ ስለ ኮረና ቫይረስ እንዳስረዱት፣ ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሰው ልጆች ላይ የመጣ ዓለም አቀፍ ፈተና ነው፡፡ ነገሮች ምን እንደሚሆኑ መገመት የሚከብድበት አስቸጋሪ ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ ምንም እንኳን ቫይረሱ የሚያደርሰው ጉዳት ሁለንተናዊ መልክ ቢኖረውም ትምህርት የአንድን አገር መፃኢ ዕድል ከሚወስኑ ዓበይት ጉዳዮች ውስጥ አንዱ በመሆኑ፣ ወረርሽኙ በትምህርት ላይ የሚያደስረው ጉዳት ብዙ ነገሮችን ሊያፋልስ እንደሚችል ሥጋታቸውን ይገልጻሉ፡፡
በመጀመሪያ ደረጃ የኮሮና ቫይረስ በጤና ላይ ሊያደርስ በሚችለው አስከፊ ጉዳት ምክኒያት፣ እንደማንኛውም የማኅበረሰብ ክፍል ተማሪዎች፣ መምህራንና የትምህርት አመራሩ ተጋላጭ የሚሆኑበት ዕድል ስላለ ህልውናቸውን አደጋ ላይ ይጥለዋል፡፡ ከዚህ ባለፈ ትምህርት በጊዜ የተከፋፈሉ ሒደቶችን የሚከተል በመሆኑ፣ እንዲህ ያለ ሁኔታ ሲያጋጥምና አጠቃላይ የትምህርት ሥርዓቱ መስተጓጎል ሲገጥመው ደግሞ የሚፈጥረው ጫና ከባድ ነው ሲሉ ለሪፖርተር መጽሔት ተናግረዋል፡፡ “የትግበራ ጊዜያቸውን ጠብቀው መከወን ባለመቻላቸውና ምዘናዎች በወቅቱ ሳይሰጡ ስለሚቀሩ፣ ዓመታዊ የትምህርት ሰሌዳው ላይ መስተጓጎል ስለሚፈጥር ይህንን ማስተካከል ለቀጣይ የትምህርት ሥራው ትልቅ ፈተና እንደሚሆን መገመት አይከብድም፤” በማለት ይናገራሉ፡፡
ዛሬ ትምህርት ቤቶች ሕንፃቸው ብቻ ቀርቶ በድን ሆነዋል፡፡ ተማሪዎች ተሰብስበው ትምህርት ይቀስሙባቸው የነበሩ የመማሪያ ክፍሎች በወንበር ብቻ ተሞልተው ሕይወት አልባ ሆነዋል፡፡ ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉ የተላለፈው ውሳኜ ድንገተኛ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ አብዛኞቹ ተማሪዎች ስለተፈጠረው ነገር በቂ ግንዛቤ ሳይኖራቸው ነው ትምህርት ተቋርጦ ወደ የቤታቸው የተሸኙት፡፡ ወደ ትምህርት ቤት መቼ እንደሚመለሱ እንኳን በማያውቁበት ሁኔታ ይህ ድንገተኛ ችግር መከሰቱ፣ በተማሪዎች ሥነ ልቦና ላይ ትልቅ ችግር እንደሚፈጥርም ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
ወ/ሮ ትዕግስት ገብረ መድኅን በፍሊፐር ኢንተርናሽናል ትምሀርት ቤት የሥነ ልቦና ባለሙያና የተማሪዎች ልዩ ድጋፍ አስተባባሪ ናቸው፡፡ ከሪፖርተር መጽሔት ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ እንዳስረዱት ’’ምንም እንኳን ትምህርት ቤቶቹ ለተማሪዎቻቸው ግዛቤን ለማስጨበጥ እንደሄዱበት ርቀት ቢለያይም፣ ሁኔታው ለተማሪዎች በተለይ ለሕፃናት እጅግ ከባድ ስሜት እንደሚፈጥርባቸው ግልጽ ነው፡፡ ስለቫይረሱ በቂ ግንዛቤ ሳያገኙና ሳይረዱት ከትምህርት ተስተጓጉለው በቤት በሚያሳልፉበት ጊዜ እጅግ ለከፋ ጭንቀትና ድብርት ሊጋለጡ የሚችሉበት እድል ሰፊ ነው’’ በማለት አብራርተዋል፡፡
ልጆች በቤት ውስጥ በሚያሳልፉበት ጊዜ አንድም ወረርሽኙ በሚፈጥርባቸው ሥጋትና ፍርሀት፣ ከትምህርት ቤትና ከጓደኞቻቸው ጋር የነበራቸው መስተጋብር ድንገት በመቋረጡ፣ በሌላ በኩል ይህ አስቸጋሪ ሁኔታ መቼና እንዴት እንደሚልያፍ ባለመረዳት ውስጥ ሆነው አስቸጋሪ ጊዜ እያሳለፉ እንደሆነ ወላጆች ሊረዱ ይገባል ሲሉ ወይዘሮ ትዕግስት ያስረዳሉ፡፡ አክለውም በዚህ ወቅት ስለ ኮሮና ቫይረስ ለልጆች እንደየ ዕድሜያቸው በሚገባቸው ቋንቋ አስፈላጊውን መረጃ መስጠት፣ ልጆች በቤት ውስጥ ረጅም ሰዓት ማሳለፍ ከዕድሜያቸው አንጻር ከባድ መሆኑን በመገንዘብ፣ የሚማሩባቸውንና የሚያዝናኗቸውን ተግባራት ማመቻቸት፣ ከመቼውም ጊዜ ባለፈ ወደ ልጆች ቀረብ በማለት እንደየ ስሜታቸው ማማከርና ማወያየት ከወላጆች የሚጠበቁ ተግባራት ናቸው በማለት አስገንዝበዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ወረርሽኙ የትምህርት ሥርዓቱን ከሚጎዳባቸው መንገዶች አንዱ የትምህርት መመዘኛ ፈተናዎችን መስጠት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በየክፍል ደረጃዎች የሚሰጡ ማጠቃለያ ፈተናዎች እንዳሉ ሆኖ፣ በተለይ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚሰጡት የስምንተኛና የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሔራዊ ፈተናዎች፣ በታቀደላቸው ጊዜ አለመሰጠታቸው በተፈታኞቹ ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት ባለፈ፣ አጠቃላይ የትምህርት ሒደቱን በእጅጉ ይጎዳዋል፡፡ ወረርሽኙ የሚቆምበት ጊዜና የሚያደርሰው ጉዳት በውል ባልታወቀበት በዚህ ጊዜ፣ በትምህርት ካሌንደር መሠረት ቀን ተቆርጦላቸው የነበሩት እነዚህ ፈተናዎች በምን መልኩ ይሰጣሉ የሚለው ጉዳይ እስካሁን መልስ አላገኘም፡፡

ትምህርት ሚኒስቴር
የትምህርት ቤቶችን መዘጋት ተከትሎ ሌላው አከራካሪ ጉዳይ የግል ትምህርት ቤቶች የትምህርት ቤት ክፍያ ሲሆን፣ አንዳንድ ወላጆች ትምህርት ቤቶች ተዘግተው ተማሪዎች ከትምህርት ውጭ በሆኑበት ሁኔታ፣ ወርኃዊ ክፍያ መጠየቅ አይገባንም ሲሉ ይሞግታሉ፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር በበኩሉ የግል ትምህርት ቤቶች ክፍያን በተመለከተ ትምህርት ቤቶች ከወላጆች ጋር ምክክር አድርገው፣ ውሳኔ ላይ እንዲደርሱ አቅጣጫ ያስቀመጠ ሲሆን፣ ወላጆች የወርኃዊ ክፍያዎችን ከ50 እስከ 75 በመቶ ብቻ እንዲከፍሉ የሚል መመሪያ ማስተላለፉ ይታወቃል፡፡
ወ/ሮ የትናየት ደሳለኝ በአነስተኛ ንግድ የተሰማሩ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ ሲሆኑ፣ ሁለት ልጆቻቸውን በአንድ የግል ትምህርት ቤት ውስጥ እንደሚያስተምሩ ለሪፖርተር መጽሔት ገልጸው፣ አገልግሎት ሳይሰጥ ክፍያ መጠየቅ አግባብ አለመሆኑንና ሊታሰብበት አንደሚገባ ይገልጻሉ፡፡ “በዚህ ሰዓት ገንዘብ አምጡ ብሎ ወላጆችን ማስጨነቅ ተገቢ አይመስለኝም፤” የሚሉት ወ/ሮ የትናየት፣ በወረርሽኙ ምክንያት ንግዳቸው እጅግ እንደተዳከመና ወርኃዊ ገቢያቸው በእጅጉ በመጎዳቱ የቤት ኪራይ ለመክፈልና ልጆቻቸውን ለመመገብ እንኳን እንደከበዳቸው ይናገራሉ፡፡ ትምህርት ቤቶች መጠነኛ የክፍያ ማሻሻያ ቢያደርጉም በርካታ ወላጆች ከገቢያቸው አንጻር ለመክፈል እንደሚቸገሩም ወ/ሮ የትናየት ይገልጻሉ፡፡ ይሁን አንጂ ትምህርት ቤቶች በበኩላቸው ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጫና ላይ እንደሚገኙ በመግለጽና የመምህራንን ደመወዝ እየከፈሉ ለመቀጠል የተማሪዎችን ክፍያ መሰብሰብ እንዳለባቸው እየገለጹ ነው፡፡ ለመምህራን ደመወዝ ለመክፈል ሌላ ገቢ ስለሌላቸው ወላጆችም የጊዜውን ሁኔታ ከግምት ውስጥ ሊያስገቡ እንደሚገባ እየገለጹ ነው፡፡ ምንም እንኳን ኮሮና ቫይረስ በአገር ደረጃ መከሰቱ ከታወቀ ገና ሁለት ወር የሆነው ቢሆንም መምህራን የሚሠሩባቸው ትምህርት ቤቶች “ከወላጆች ክፍያ ስላልሰበሰብን ደመወዝ መክፈል አንችልም” በማለታቸው ምክንያት ደመወዝ እንዳልተከፈላቸው አንዳንድ መምህራን እየተናገሩ ነው፡፡
አንዳንድ የግል ትምህርት ቤቶች ሥራቸውን የሚያከናውኑት ሕንፃዎችን በውድ ዋጋ ተከራይተው እንደሆነ በመግለጽ፣ የተማሪዎችን ክፍያ ካልሰበሰቡ ከፍተኛ ኪሳራ ላይ እንደሚወድቁና በዚህ ሁኔታ ሥራው ላይ ለመቆየት እንደሚያዳግታቸው ጭምር እየተናገሩ ነው፡፡
መምህር ታደሰ ጥበበ፣ በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ የሚገኝ የኪድስ ፓራዳይዝ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ ናቸው፡፡ በኮሮና ቫይረስ ምክንያት የተቋረጠውን ትምህርት በተወሰነ መልኩም ቢሆን ለማስቀጠል ቴሌግራም ዋትስአፕ እና ሌሎች ማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎችን በመጠቀም የትምህርት ይዘቶችንና ጥያቄዎችን በወላጆች አማካይነት ለተማሪዎች ለማድረስ ጥረት እያደረጉ መሆኑን ጠቅሰው፣ እስካሁን 61 ከመቶ የሚሆኑ የተማሪዎች ወላጆችን ተደራሽ ማድረግ የተቻለ መሆኑንና ቀሪዎቹ ወላጆች በተለያዩ ምክንያቶች አገልግሎቱን መጠቀም እንዳልቻሉ ይገልጻሉ፡፡ ይህንንም ችግር ለመቅረፍ የትምህርት ይዘቶችን በወረቀት በማባዛት እንዲደርሳቸው ማድረጋቸውንም አስረድተዋል፡፡
ትምህርት ቤቶቹ ምንም እንኳን ለትርፍ የተቋቋሙ ቢሆንም፣ በከተማዋ የሚገኙ የግል ትምህርት ቤቶች ከመንግሥት ትምህርት ቤቶች በላይ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎችን በመያዝ፣ ትምህርትን በተሻለ ጥራት በመስጠት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው መሆኑን በመግለጽ፣ በዚህ ወቅት ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ውስጥ በመግባታቸው እንደ ተቋም ለመቀጠል የማይችሉበት ደረጃ ላይ የሚደርሱ ትምህርት ቤቶች መኖራቸውን አንስተዋል፡፡ ይህንን ችግርም ለመቅረፍ መንግሥት ተገቢውን መረጃ በመሰብሰብ ከፍተኛ የኪራይ ጫና ያለባቸውንና አገልግሎታቸውን በአነስተኛ ክፍያ የሚሰጡ ተቋማት በመለየት፣ ከችግራቸው ማገገም እንዲችሉ በየደረጃው አስፈላፈጊው ድጋፍ ሊደርግላቸው ይገባል ብለዋል፡፡ የግብር እፎይታን ጨምሮ የረጅም ጊዜ ብድር እንዲያገኙ ቢደረግ ከችግራቸው ማገገም እንደሚችሉም ጠቁመዋል፡፡፡
ወረርሽኙ በመምህራንም ላይ በርካታ አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በማሳደር ላይ ነው። ጉዳዩን ከገቢ አንፃር ብንመለከተው በርካታ መምህራን ኑሯቸውን ለመደገፍ በትርፍ ጊዜያቸው ይሠሩት የነበረው ተማሪዎችን በግላቸው ያደርጉት ይነበረው የቤት-ለ-ቤት ማስጠናትና ሌሎች የትርፍ ጊዜ ሥራዎች ሙሉ በሙሉ ተቋርጠዋል። ይህም የቤት ኪራይና ሌሎችን ወጪዎቻቸውን እንዳይሸፍኑ አድርጓቸዋል።
በተጨማሪም በሸቀጣ ሸቀጥ ምርቶች ላይ የተስተዋለው ከፍተኛ ጭማሪ መምህራንን በእጅጉ እንደጎዳቸው የሚገልጹት ደግሞ አቶ ጌታየ አሰፋ በዩኒቲ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የአካደሚክ ድጋፍ አገልግሎት ሥራ አስኪያጅ ናቸው፡፡ እሳቸው የሚሠሩበት ተቋም የሚማሩ ተማሪዎች በማኅበራዊ መገናኛ መረቦች ወይም ድረ ገጾች አማካይነት በመጠቀም ትምህርቱን ተደራሽ ለማድረግ ጥረቶችን እያደረገ ነው፡፡ በመምህራን የተዘጋጁ ትምህርቶችን (ኖቶች)፣ ጥያቄዎችን በቴሌግራም ቻናል በተለያዩ ቻናሎች አማካይነት ለተማሪዎች እየላከ እንደሆነና በዚህም በርካታ ተማሪዎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ይገልጻሉ፡፡
አቶ ጌታየ እንደሚሉት ከሆነ፣ እንደ አጠቃላይ ወረርሽኙ ድንገተኛ በመሆኑ ምክንያት በቂ የዝግጅት ጊዜ አልነበረም። በመሆኑም ተማሪዎችና መምህራን ከትምህርት ቤት እንዲቀሩና ቤት እንዲቀመጡ ከተደረገ በኋላ ትምህርት ቤቶች ይህን መሰሉን ተግባር ለማከናወን ቀላል አይደለም። ሁኔታው በፖሊሲ የተደገፈም ስላልሆነ ፍላጎቱና አቅሙ ካላቸው ተቋማት በስተቀር ጥረቱ ውስንነት እንዳለበት ይናገራሉ፡፡ “እዚህ ላይ ምን ያህሎቹ የአገራችን ትምህርት ቤቶች የኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚ ናቸው? ምን ያህሉ ወላጅ፣ ተማሪ፣ መምህርና ሌላው ለቴክኖሎጂ ቅርበት አለው? ብለን ራሳችንን ብንጠይቅ፣ አይደለም ገጠሩን የአገራችንን ተማሪ በዋና ከተማችን አዲስ አበባ የሚገኙ ተማሪዎችን እንኳ በዚህ መልኩ በውል ማስተማር እንደማንችል ግልጽ ነው፤” በማለት አቶ ጌታየ ለሪፖርተር መጽሔት ተናግረዋል፡፡ ተአምር ተፈጥሮ ሁሉንም የአዲስ አበባ ከተማ ተማሪዎች መድረስ ተችሏል ቢባል እንኳን፣ ከ80 በመቶ በላይ ገጠር የሚኖር ሕዝብና ተማሪ ስላለን ታላቅ የፍትሐዊነት ጥያቄ እንደሚያስነሳ ጠቁመዋል። በመሆኑም ጥረቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እየተመከረ ባለበት አግባብ፣ ቴክኖሎጂውን መጠቀሙ ጥሩ ቢሆንም ሁሉንም ያላካተተ ከመሆኑ አንፃር አመርቂና ውጤታማ ነው የሚል እምነት እንደሌላቸው በመግለጽ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በአጠቃላይ የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ የትምህርት ሥርዓቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲፋለስና በሁሉም አካላት ላይ ጫና እየፈጠረ የሚገኝ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ችግር ነው፡፡ የትምህርት ሥርዓቱ የሚያገግምበት ሁኔታና ፍጥነት፣ ወረርሽኙ የሚያደርሰው የጉዳትና መጠን የሚወስን መሆኑ እንዳለ ሆኖ ወረርሽኙ በየትኛውም ሁኔታ ማለፉ አይቀርም፡፡ ችግሩ ካለፈ በኋላ እንዴት መቀጠል አለብን የሚለው ላይ አንደ አገር ዝግጅት መደረግ አለበት፡፡ የትምህርት ሚኒስቴርና የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር የተቀናጀ አገራዊ ዕቅድ አዘጋጅተው በየደረጃው ያሉትን የትምህርት መዋቅሮች በመጠቀም የተቀናጀ ሥራ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ እንደ ኮሮና ቫይረስ ያሉ ድንገተኛ ወረርሽኞች ሲከሰቱ ሊያደርሱ የሚችሉት ጉዳት በቀላሉ ሊገመት የሚችል ባለመሆኑ፣ ሁሉም ዜጋ አንድ ሆኖና ተባብሮ ችግሩን በሚያልፍበት ጉዳይ ላይ መሥራት አለበት፡፡ የወረርሽኝ ችግር በሕግና በመመሪያ ብቻ የሚፈታ ባለመሆኑ ለመከላከልም ሆን ለመቆጣጠር የሁሉንም ማኅበረሰብ ተሳትፎ ይጠይቃል፡፡ በመሆኑም ሁሉም ዜጋ ሳይዘናጋና ችላ ሳይል ከሕክምና ባለሙያዎች የሚነገሩ ምክሮችን፣ መከላከያ መንገዶችንና መንግሥት በአዋጅ ጭምር ያስተላለፋቸውን መመሪያዎች ተገባራዊ ማድረግ አለበት፡፡
ምንም እንኳን ወቅቱ በአገርም ሆነ በዓለም ከፍተኛ የሆነ የኢኮኖሚ ድቀትና ቀውስ ማምጣቱ የሚታወቅ ቢሆንም፣ መምህራን ለቀጣዩ ትውልድ ዕውቀት ሰጭና አገር ተረካቢ ትውልድ አፍሪ ከመሆናቸውም ሌላ፣ ወላጆች ለትምህርት ቤቶች ከሚከፍሉት ወርኃዊ ክፍያ ላይ ተከፍሏቸው ዜጋን የሚያገለግሉ መሆናቸውን መንግሥትም ሆነ ወላጆች ሊገነዘቡት ይገባል፡፡