ዓለም በ21ኛው ክፍለ ዘመን ፈተናዋ በዝቷል፡፡ የእርስ በርስ ጦርነት፣ መጐዳዳት፣ መገዳደል፣ ስደት፣ መፈናቀል፣ ድርቅ፣ የአየር ንብረት መቀያየር፣ በአገሮች መካከል ከቃላት ጦርነት ጀምሮ በጦር መሣሪያ የታገዘ ውጊያ ማድረግ የዕለት ተዕለት ተግባራት ከሆኑ ሰነባብተዋል፡፡ በነዚህ ሒደቶች ሁሉ የሰው ልጆች እንደ ቅጠል በየቀኑ እየገረገፉ ነው፡፡ የሚገርመው ነገር በነዚህ የሰው ልጅ ለሰው ልጅ እልቂት ፈጣሪ በሆነበት ወቅት አንዱ ከአንዱ፣ ወይም አቅም ያነሰው ከጉልበተኛው አምልጦ ለመዳን የተሻለ መጠጊያ ይሆነኛል ወዳለው ሌላኛው ሀገር ይሰደዳል፡፡ በየብስና በባሕር በሚያደርገው ስደት ያለቀው አልቆ የተረፈው የስደት መዳረሻ አድርጐ በተጓዘበት ሀገር ይደርሳል፡፡ ምንም እንኳን አቀንቃኙ “ማን እንደናት ማን እንዳገር” እንዳለው፣ የስደት ሀገር እንደ ትውልድ ሀገር ባይሆንም፣ እስትንፋስን ጠብቆ የተሻለ ጊዜ ከመጣ ለመሸጋገሪያ ይጠቅማል በሚልና የደረሰበትን የራሱን፣ የቤተሰቡን፣ የወገኑንና የአገሩን መከራና ስቃይ እያሰላሰለ ቢሆንም፣ “ተመስገን” ማለቱና ሕይወት መቀጠሏ አይቀርም፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው የመጣበትን አደጋ በዛም በዚህ ብሎ ማምለጥ የሚችልበት እድልና አጋጣሚ በማግኘቱ ነው፡፡ እነዚህ እድሎች የማይኖሩበት አጋጣሚ ሲፈጠርስ ምን ማድረግ ይቻላል? መልሱ ምንም ነው፡፡
የሰው ልጅ በሠራቸው ከጅምላ ጨራሽ እስከ ነፍስ ወከፍ የጦር መሣሪያዎች አንዱ በሌላው ላይ ለመንገሥ በሚያደርገው ሽኩቻ፣ ዓለም በቀውስ ውስጥ ሆና መቀጠል እንዳለ ሆኖ፣ ሁሉንም እኩል ያደረገና ማንም በማንም ላይ ኃይሉን የማያሳይበት ሌላ የዓለም ፈተና ወረሽኝ ከተከሰተ ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ኖቭል ኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ 19) በቻይና ሁቤ ግዛት ውሃን ከተማ ውስጥ ባለፈው ዲሴምበር መጨረሻ ላይ የተከሰተው ይህ ወረርሽኝ በአራት ወራት ውስጥ ከ290,000 በላይ ሰዎችን ሕይወት አጥፍቶ ከ4.2 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ደግሞ የቫይረሱ ተጠቂዎች እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ ኮሮና ቫይረስ እስከ አሁን በ212 አገሮች ውስጥ የተዳረሰ ሲሆን፣ በተለይ አሜሪካን፣ አውሮፓን፣ መካከለኛው ምሥራቅና የእስያን አገሮች በከፍተኛ ሁኔታ አጥቅቷል፡፡ በተጠቀሱት አገሮች የሞቱና በቫይረሱ የተጠቁ ሰዎች ውስጥ ከፍተኛውን ቁጥር የያዙት የእነዚሁ አገሮች ዜጐች ናቸው፡፡ ወረርሽኙ በአፍሪካ ያደረሰው ጉዳት ቀላል አይደለም፡፡ ከተጠቀሱት ሌሎች አገሮች አንፃር ሲወዳደር ዝቅ ያለ በመሆኑ እንጂ፡፡ በአፍሪካ ከ60,000 በላይ ሰዎች በቫይረሱ የተጠቁ ሲሆን፣ ከ22ዐዐ በላይ ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸው አልፏል፡፡ ደቡብ አፍሪካ፣ ግብፅና አልጀሪያ በወረርሽኙ በከፍተኛ ሁኔታ የተጠቁ ሲሆኑ፣ ሌሎቹም የአፍሪካ አገሮች የጥቃቱ ሰለባ ከመሆን አላመለጡም፡፡ በኢኮኖሚያቸውም ሆነ በጦረኝነታቸው የምድሩን አልፈው ጨረቃን የሚመራመሩት ኃያላንን ሁሉ መግቢያ መውጫ ያሳጣው ኮሮና ቫይረስ፣ ዓለም አንድ አይነት አስተሳሰብና አቅም (ጥራቱ ቢለያይም) እንዲኖራቸው አድርጓል፡፡
ይህ ወረርሽኝ እስከ አሁን ምንም ዓይነት ፈዋሽ መድኃኒት አልተገኘለትም፡፡ ሁሉም አገሮች ከዚህ አስከፊ ወረርሽን ለመትረፍ ማድረግ ያለባቸው ተመሳሳይ ድርጊቶች እጅን ደጋግሞ መታጠብ፣ የእስትንፋስ አካላትን በእጅ አለመነካካት፣ መራራቅና ከተቻለ በቤት ወስጥ መቆየት ናቸው፡፡ በአሜሪካም ሆነ በኢትዮጵያ የድርጊቱ ጥራት ይለያይ እንጂ መደረግ ያለበት የወረርሽኙ መከላከያ መንገድ ተመሳሳይ ነው፡፡
የጤና ሚኒስቴር ግንቦት 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ባወጣው መረጃ፣ በኢትዮጵያ ኮሮና ቫይረስ መከሰቱ ከታወቀበት መጋቢት 4 ቀን 2ዐ12 ዓ.ም. ጀምሮ አምስት ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ፣ 261 ሰዎች በቫይረሱ ተጠቅተዋል፡፡ 106 ሰዎች ደግሞ አገግመዋል፡፡ ከሌሎቹ አገሮችና ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር፣ የአኗኗር ዘይቤና አጠቃላይ ሁኔታ አንፃር፣ በሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ የደረሰው አደጋ በጣም አስደንጋጭ ባይሆንም አሳሳቢ ነው፡፡ ምክንያቱም የቫይረሱ መኖሩ በተነገረበት ወቅት የነበረው የሕዝብ ሁኔታና ከአንድ ወር ቆይታ በኋላ ያለው ሁኔታ ፈጽሞ የተለየ በመሆኑ በእጅጉ ያሳስባል፡፡ በመጀመሪያው አካባቢ በጤና ባለሙያዎች ይነገር የነበረውን የምክር አገልግሎት በመቀበልና በመተግበር ረገድ የተሻለ ነበር፡፡ መንግሥትም የተለያዩ መመሪያዎችን በማውጣት እንዲተገበር ያደርግ የነበረው ጥረት አጀማመሩ ጥሩ የነበረ ቢሆንም፣ እየላላ በመምጣቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እስከማወጅ ደርሷል፡፡ ሕዝቡ ግን ድንጋጤውንም ሆነ ፍርሃቱን ከአንድ ወር በላይ ሊያስቀጥለው አልቻለም፡፡ በተለይ ከፋሲካ (ትንሣኤ) በዓል አካባቢ ጀምሮ ሕዝቡ የዘወትር ሕይወቱን በመቀጠል ከመጨባበጥና መተቃቀፍ ባለፈ ተጠጋግቶ መተረማመሱ፣ የፊት መሸፈኛ ማስክ ሳያደርጉ መነጋገርና ሌሎችም ነባር ግንኙነቶች ቀጥለዋል፡፡ ታዲያ ይህ ድፍረት የተሞላበት አካሄድና ቸልተኝነት ሰሞኑን ከጤና ሚኒስቴር እየተነገረን ያለውን በቫይረሱ የተጠቁ ወገኖች ቁጥር ምን ያህል እያሻቀበ እንደሆነ መስማትና ማየት በቂ ነው፡፡
አሁንም ቢሆን ጊዜው አልረፈደም፡፡ ሁሉም የሚመለከተውን ብቻ በመተግበር ከተንቀሳቀሰ ቢያንስ ወረርሸኙ ባለበት መግታት ይቻላል፡፡ በጤና ባለሙያዎች እየተነገሩ ያሉ የወረርሽኙ ምልክቶች እንዳሉ ሆነው፣ ምንም ዓይነት ምልክት፣ ንክኪም ሆነ የውጭ የጉዞ ታሪክ በሌለው ሰውም ላይ ቫይረሱ እየተገኘ በመሆኑ፣ ምልክቶቹ የሌለባቸው ሰዎች ጤነኛ ናቸው ለማለት የማያስደፍር ደረጃ ላይ እየተደረሰ መሆኑን የሚያሳይ ከመሆኑ አንፃር፣ ቸልተኝነት፣ ምክር አለመስማት፣ ድፍረት የተሞላበት እንቅስቃሴ ከሞት ስለማያድን ሁሉም ይጠንቀቅ፣ መሥራት ያለበትን ይሥራ፣ ይተግብር፡፡ መንግሥትም እንደ መንግሥት አገርን ከማስተዳደርና አስተዳደራዊ ሥርዓቱ እንዴት መቀጠል እንዳለበት መሥራት የሚገባውን እየሠራ ዋና ትኩረቱን ግን በወረርሽኙ ላይ ማድረጉን መዘንጋት የለበትም፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በተለይ ከምርጫ ጋር ተያይዞ አጣብቂኝ ሁኔታ ውስጥ መሆኗ ይታወቃል፡፡ ምንም እንኳን ከመስከረም 3ዐ ቀን 2ዐ13 ዓ.ም. በኋላ ነባሩ የመንግሥት ሥልጣን ማብቂያ ቢሆንም፣ ቀጣዩ ምርጫ እስከሚደረግ ድረስ የማሸጋገሪያ መንገዶች ስላሉ በሰከነና ዴሞክራሲያዊ የሆነ አካሄድን በመተግበር፣ አገርን ማስቀጠልና ሕዝብንም ማስተዳደር ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ ይኸንን አይምሬ ወረርሽኝ መከላከልና ሕዝብን ማዳን የሚቻለው፣ ለሕዝብና ለአገር ይጠቅማል ተብሎ የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማስተግበርና በመተግበር ለሕዝብ ከሕዝብ ጋር በመቆም ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ፈታኝ ጊዜያትን ለማለፍ ጥንቃቄና ብልሃትን መሣሪያ ማድረግ ግድ ይላል!